ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ዕዝራ 1 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ቂሮስ ምርኮኞቹ እንዲመለሱ ፈቀደ

1. ቂሮስ የፋርስ ንጉሥ በሆነ በመጀመሪያው ዓመት፣ እግዚአብሔር የቂሮስን መንፈስ አነሣሥቶ በመንግሥቱ ሁሉ ዐዋጅ እንዲያስነግርና ይህም በጽሑፍ እንዲሰፍር አደረገ፤ ይህ የሆነው በኤርምያስ አፍ የተነገረው የእግዚአብሔር ቃል ይፈጸም ዘንድ ነው።

2. “የፋርስ ንጉሥ ቂሮስ የሚለው ይህ ነው፤ “ ‘የሰማይ አምላክ እግዚአብሔር የምድርን መንግሥታት ሁሉ ሰጥቶኛል፤ በይሁዳ ምድር በምትገኘው በኢየሩሳሌምም ለእርሱ ቤተ መቅደስ እንድሠራ አዞኛል።

3. ከሕዝቡ መካከል በእናንተ ዘንድ የሚኖር ማናቸውም ሰው አምላኩ ከእርሱ ጋር ይሁን፤ በይሁዳ ወደምትገኘው ወደ ኢየሩሳሌም ይውጣና በዚያ ለሚኖረው አምላክ፣ ለእስራኤል አምላክ ለእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ይሥራ፤

4. ባሉበት ስፍራ የሚቀሩ በየትኛውም አገር የሚኖሩ ሰዎች ሁሉ በኢየሩሳሌም ለሚገኘው የእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ስጦታ እንዲሆን በበጎ ፈቃድ ከሚያቀርቡት መባ በተጨማሪ ብርና ወርቅ፣ ዕቃና እንስሳ በመስጠት ይርዷቸው።’ ”

5. ከዚያም እግዚአብሔር መንፈሳቸውን ያነሣሣው የይሁዳና የብንያም ቤተ ሰብ አለቆች እንዲሁም ካህናቱና ሌዋውያኑ ሁሉ ለመሄድና በኢየሩሳሌም የሚገኘውን የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ለመሥራት ተዘጋጁ።

6. ጎረቤቶቻቸውም ሁሉ በበጎ ፈቃድ ከሰጡት መባ በተጨማሪ ከብርና ከወርቅ የተሠሩ ዕቃዎችን፣ ቈሳቍስን፣ እንስሶችንና ሌሎች ጠቃሚ የሆኑ ስጦታዎችንም በመለገስ ረዷቸው።

7. ከዚህም በላይ ንጉሡ ቂሮስ፣ ናቡከደነፆር ከኢየሩሳሌም ወስዶ በአማልክቱ ቤተ ጣዖት ያኖራቸውን የእግዚአብሔርን ቤተ መቅደስ ንዋያተ ቅድሳት አወጣ።

8. የፋርስ ንጉሥ ቂሮስ በግምጃ ቤቱ ኀላፊ በሚትሪዳጡ አማካይነት ንዋያተ ቅድሳቱ እንዲመጡና በይሁዳው ገዢ በሰሳብሳር ፊት እንዲቈጠሩ አደረገ።

11. ባጠቃላይ አምስት ሺህ አራት መቶ የወርቅና የብር ዕቃዎች ነበሩ። ሰሳብሳር ምርኮኞቹ ከባቢሎን ወደ ኢየሩሳሌም ሲመለሱ ይህን ሁሉ ዕቃ ይዞ ወጣ።