ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኤርምያስ 3:8-20 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

8. ለከዳተኛ ዪቱ እስራኤል ስለ ምንዝርናዋ ሁሉ የፍች ወረቀቷን ሰጥቼ አባረርኋት። ከሓዲዋ እኅቷ ይሁዳም ይህን አይታ እንዳልፈራች አየሁ፤ ወጥታም አመነዘረች።

9. በቅሌቷም ምድሪቱን አረከሰች፤ ከድንጋይና ከግንድ ጋር አመነዘረች፤

10. ይህም ሁሉ ሆኖ ከሓዲዋ እኅቷ ይሁዳ ወደ እኔ የተመለሰችው በማስመሰል እንጂ በሙሉ ልቧ አልነበረም” ይላል እግዚአብሔር።

11. እግዚአብሔር እንዲህ አለኝ፤ “ከከሓዲዋ ይሁዳ ይልቅ ከዳተኛዪቱ እስራኤል ጻድቅ ሆና ተገኘች።

12. ሂድና ይህን መልእክት ወደ ሰሜን እንዲህ ብለህ ተናገር፤“ ‘ከዳተኛዪቱ እስራኤል ሆይ፤ ተመለሽ’ ይላል እግዚአብሔር፤‘እኔ መሓሪ ስለ ሆንሁ፣ከእንግዲህ በቍጣ ዐይን አላይሽም’ይላል እግዚአብሔር። ‘ለዘላለም አልቈጣም።

13. በአምላክሽ በእግዚአብሔር ላይ በማመፅሽ፣ክብርሽንም ለእንግዶች አማልክት፣በየለምለሙ ዛፍ ሥር አሳልፈሽ በመስጠት፣ለእኔ ባለመታዘዝሽ፣በደለኛ መሆንሽን ይህን አንድ ነገር ብቻ እመኚ’ ”ይላል እግዚአብሔር።

14. “ከዳተኛ ልጆች ሆይ፤ እኔ ባለቤታችሁ ነኝና ተመለሱ” ይላል እግዚአብሔር፤ “ከአንድ ከተማ አንድ፣ ከአንድ ነገድ ሁለት መርጫችሁ ወደ ጽዮን አመጣችኋለሁ።

15. እንደ ልቤም የሆኑ፣ በዕውቀትና በማስተዋል የሚመሯችሁን እረኞች እሰጣችኋለሁ።

16. ቍጥራችሁ በምድሪቱ እጅግ በሚበዛበት ጊዜም ይላል እግዚአብሔር፤ “በዚያ ዘመን፣ ‘የእግዚአብሔር የኪዳኑ ታቦት’ ብለው ከእንግዲህ አይጠሩም፤ ትዝ አይላቸውም፤ አያስታውሱትምም፤ አይጠፋም፤ ሌላም አይሠራም።

17. በዚያ ጊዜ ኢየሩሳሌምን፣ ‘የእግዚአብሔር ዙፋን’ ብለው ይጠሯታል፤ መንግሥታትም ሁሉ የእግዚአብሔርን ስም ለማክበር በኢየሩሳሌም ይሰበሰባሉ፤ የክፉ ልባቸውንም እልኸኝነት ከእንግዲህ አይከተሉም።

18. በዚያን ዘመን የይሁዳ ቤትና የእስራኤል ቤት በአንድነት ሆነው ከሰሜን ምድር ለአባቶቻቸው ርስት አድርጌ ወደ ሰጠኋቸው ምድር ይመጣሉ።

19. “እኔም፣“ ‘የተመረጠችውን ምድር፣የትኛውም ሕዝብ ያላገኘውን የተዋበች ርስት ልሰጥሽ፣እንደ ወንዶች ልጆቼ ምንኛ በደስታ ልቍጠርሽ” አልሁ፤‘አባቴ’ ብለሽ የምትጠሪኝ፣እኔንም ከመከተል ዘወር የማትይ መስሎኝ ነበር።

20. የእስራኤል ቤት ሆይ፤ ለባሏ ታማኝ እንዳልሆነች ሚስት፣ስታታልሉኝ ኖራችኋል፤”ይላል እግዚአብሔር።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኤርምያስ 3