ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኢዮብ 41:6-21 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

6. ነጋዴዎችስ በእርሱ ላይ ይከራከራሉን?ለቸርቻሪዎችስ ያከፋፍሉታል?

7. ቈዳው ላይ አንካሴ ልትሰካ፣ጭንቅላቱንም በዓሣ መውጊያ ጦር ልትበሳ ትችላለህን?

8. እርሱን እስቲ ንካው፣ግብግቡን ታስታውሳለህ፤ ከቶም አያላምድህም።

9. እርሱን በቍጥጥር ሥር አውላለሁ ማለት ዘበት ነው፤በዐይን ማየት እንኳ ብርክ ያስይዛል።

10. ሊቀሰቅሰው የሚደፍር የለም፤ማን ፊቱ ሊቆም ይችላል?

11. ነክቶት በሰላም የሚሄድ ማን ነው?ከሰማይ በታች ማንም የለም።

12. “ስለ ብርታቱና ስለ አካላቱ ውበት፣ስለ እጅና እግሩ ከመናገር አልቈጠብም።

13. የደረበውን ልብስ ማን ሊያወልቅ ይችላል?ማንስ ሊለጒመው ወደ መንጋጋው ይቀርባል?

14. አስፈሪ ጥርሶቹ የተገጠገጡበትን፣የአፉን ደጅ ማን ደፍሮ ይከፍታል?

15. ጀርባው፣ አንድ ላይ የተጣበቁ፣የጋሻ ረድፎች አሉት፤

16. እጅግ የተቀራረቡ ስለሆኑ፣ነፋስ በመካከላቸው አያልፍም፤

17. እርስ በርስ የተገጣጠሙ ናቸው፤አንዱ ከአንዱ ጋር ተጣብቆአልና ማንም ሊለያያቸው አይችልም።

18. እንጥሽታው የብርሃን ብልጭታ ያወጣል፤ዐይኖቹም እንደ ማለዳ ጮራ ናቸው።

19. ከአፉ ፍም ይወጣል፤የእሳት ትንታግ ይረጫል።

20. በሸምበቆ ማገዶ ላይ ከተጣደ ድስት እንደሚወጣ እንፋሎት፣ከአፍንጫው ጢስ ይትጐለጐላል።

21. እስትንፋሱ ከሰል ያቀጣጥላል፤የእሳትም ነበልባል ከአፉ ይወጣል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኢዮብ 41