ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኢዮብ 30:1-13 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. “አሁን ግን በዕድሜ ከእኔ የሚያንሱ፣ከመንጋዬ ጠባቂ ውሾች ጋር እንዳይቀመጡ፣አባቶቻቸውን የናቅኋቸው፣እነዚህ ይሣለቁብኛል።

2. ጒልበት የከዳቸው፤የክንዳቸው ብርታት ምን ፋይዳ ይሞላልኝ ነበር?

3. ከችጋርና ከራብ የተነሣ ጠወለጉ፤ሰው በማይኖርበት በረሓ፣በደረቅም ምድር በሌሊት ተንከራተቱ።

4. ከቍጥቋጦ ምድር ጨው ጨው የሚል አትክልት ለቀሙ፤ምግባቸውም የክትክታ ሥር ነበር።

5. ከኅብረተ ሰቡ ተለይተው ተባረሩ፤ሰዎች እንደ ሌባ ይጮኹባቸዋል።

6. በዐለት መካከል በምድር ጒድጓድ፣በደረቅ ሸለቆ ዋሻ ውስጥ ለመኖር ተገደዱ።

7. በጫካ ውስጥ ያናፋሉ፤በእሾሃማ ቍጥቋጦ መካከልም ይታፈጋሉ።

8. ስማቸው የማይታወቅ አልባሌ ናቸው፤ከምድሪቱም ተባረዋል።

9. “አሁን ግን ልጆቻቸው በዘፈን ይሣለቁብኛል፤በእነርሱም ዘንድ መተረቻ ሆኛለሁ።

10. ይጸየፉኛል ወደ እኔም አይቀርቡም፤ያለ ምንም ይሉኝታ በፊቴ ይተፋሉ።

11. እግዚአብሔር የቀስቴን አውታር ስላላላውና በመከራም ስለ መታኝ፣በፊቴ መቈጠብን ትተዋል።

12. በቀኜ በኩል ባለጌዎች ሆ! ብለው ተነሡብኝ፤ለእግሬም ወጥመድ ዘረጉ፤የዐፈር ድልድልም አዘጋጁብኝ።

13. መንገድ ዘጉብኝ፤የሚገታቸው ሳይኖር፣ሊያጠፉኝ ተነሡ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኢዮብ 30