ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኢያሱ 4:3-11 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

3. እንዲሁም ከዮርዳኖስ ወንዝ መካከል ልክ ካህናቱ ከቆሙበት ስፍራ ዐሥራ ሁለት ድንጋይ አንሥተው በመሸከም ከእናንተ ጋር እንዲሻገሩና ዛሬ በምታድሩበት ቦታ እንዲያኖሯቸው ንገራቸው።”

4. ስለዚህ ኢያሱ ከእያንዳንዱ የእስራኤል ነገድ የሾማቸውን ዐሥራ ሁለት ሰዎች ጠራ፤

5. እንዲህም አላቸው፤ “ከአምላካችሁ ከእግዚአብሔር ታቦት ፊት ቀድማችሁ ወደ ዮርዳኖስ ወንዝ መካከል ዕለፉ፤ እያንዳንዳችሁም በእስራኤል ነገድ ቊጥር አንዳንድ ድንጋይ በትከሻችሁ ተሸከሙ፤

6. ይህም በመካከላችሁ ምልክት እንዲሆናችሁ ነው። ወደ ፊት ልጆቻችሁ፣ ‘እነዚህ ድንጋዮች ምንድን ናቸው?’ ብለው ቢጠይቋችሁ፣

7. የዮርዳኖስ ወንዝ በእግዚአብሔር የቃል ኪዳኑ ታቦት ፊት መቆሙን፤ እንዲሁም ታቦቱ ዮርዳኖስን በሚሻገርበት ጊዜ፣ የዮርዳኖስ ወንዝ ውሃ መቆሙን፣ እነዚህ ድንጋዮች ለእስራኤል ሕዝብ የዘላለም መታሰቢያ መሆናቸውን ንገሯቸው።”

8. እስራኤላውያንም ኢያሱ እንዳዘዛቸው አደረጉ፤ እግዚአብሔር ለኢያሱ በነገረውም መሠረት፣ በእስራኤል ነገዶች ቊጥር ልክ ዐሥራ ሁለት ድንጋዮች ከዮርዳኖስ ወንዝ መካከል አነሡ፤ ወደ ሰፈራቸውም ይዘው በመሻገር በዚያ አኖሯቸው።

9. ኢያሱም የቃል ኪዳኑን ታቦት የተሸከሙት ካህናት ቆመውበት በነበረው በዮርዳኖስ ወንዝ መካከል ሌሎች ዐሥራ ሁለት ድንጋዮችን አቆመ፤ እነዚህም ድንጋዮች እስከ ዛሬ ድረስ በዚሁ ስፍራ ይገኛሉ።

10. ሙሴ ለኢያሱ በሰጠው መመሪያ መሠረት፣ እግዚእብሔር ለሕዝቡ እንUntitled eventዲነግር ኢያሱን ያዘዘው እስኪፈጸም ድረስ፣ ታቦቱን የተሸከሙት ካህናት በዮርዳኖስ መካከል ቆመው ቈዩ፤ ሕዝቡም ፈጥነው ተሻገሩ፤

11. ሕዝቡ ሁሉ ተሻግረው እንዳበቁ፣ የእግዚአብሔር ታቦትና ካህናቱ፣ ሕዝቡ እያዩአቸው ተሻገሩ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኢያሱ 4