ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኢዩኤል 2:5-20 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

5. ገለባ እንደሚበላ እንደሚንጣጣ እሳት፣ለጦርነት እንደ ተዘጋጀ ኀያል ሰራዊት፣የሠረገሎችን ድምፅ የሚመስል ድምፅ እያሰሙ፣በተራሮች ጫፍ ላይ ይዘላሉ።

6. በእነርሱ ፊት ሕዝቦች ይርዳሉ፤የሁሉም ፊት ይገረጣል።

7. እንደ ተዋጊዎች ድንገት አደጋ ይጥላሉ፤እንደ ወታደሮችም ቅጥርን ይዘላሉ፤ከመንገዳቸውም ሳይወጡ፣አቅጣጫ ይዘው ይጓዛሉ።

8. እርስ በርሳቸው አይገፋፉም፤እያንዳንዱ መስመሩን ጠብቆ ይሄዳል፤መስመራቸውን ሳይለቁ፣መከላከያውን ሰብረው ያልፋሉ።

9. ከተማዪቱን ይወራሉ፤በቅጥሩም ላይ ይዘላሉ፤በቤቶች ላይ ዘለው ይወጣሉ፤እንደ ሌባም በመስኮት ይገባሉ።

10. ምድር በፊታቸው ትንቀጠቀጣለች፤ሰማይም ይናወጣል፤ፀሓይና ጨረቃ ይጨልማሉ፤ከዋክብትም ከእንግዲህ ወዲያ አያበሩም።

11. በሰራዊቱ ፊት፣ እግዚአብሔር ያንጐደጒዳል፤የሰራዊቱ ብዛት ስፍር ቊጥር የለውም፤ትእዛዙንም የሚያደርግ እርሱ ኀያል ነው፤ የእግዚአብሔር ቀን ታላቅ፣እጅግም የሚያስፈራ ነው፤ማንስ ሊቋቋመው ይችላል?

12. “አሁንም ቢሆን፣በጾም፣ በልቅሶና በሐዘን፣በፍጹም ልባችሁ ወደ እኔ ተመለሱ” ይላል እግዚአብሔር።

13. ልባችሁን እንጂ፣ልብሳችሁን አትቅደዱ፤ወደ አምላካችሁ ወደ እግዚአብሔር ተመለሱ፤እርሱ መሓሪና ርኅሩኅ፣ቊጣው የዘገየና ፍቅሩ የበዛ፣ክፉ ነገር ከማምጣትም የሚታገሥ ነውና።

14. በምሕረቱ ተመልሶ፣ለአምላካችሁ ለእግዚአብሔር የሚሆነውን፣የእህል ቊርባንና የመጠጥ ቊርባን እንዲተርፋችሁ፣በረከቱን ይሰጣችሁ እንደሆነ ማን ያውቃል?

15. በጽዮን መለከትን ንፉ፤ቅዱስ ጾምን ዐውጁ፤የተቀደሰን ጉባኤ ጥሩ።

16. ሕዝቡን ሰብስቡ፤ጉባኤውን ቀድሱ፤ሽማግሌዎችን በአንድነት አቅርቡ፤ሕፃናትን ሰብስቡ፤ጡት የሚጠቡትንም አታስቀሩ፤ሙሽራው እልፍኙን ይተው፣ሙሽሪትም የጫጒላ ቤቷን ትተው።

17. በእግዚአብሔር ፊት የሚያገለግሉ ካህናት፣በመሠዊያውና በቤተ መቅደሱ አደባባይ መካከል ሆነው ያልቅሱ፤እንዲህም ይበሉ፤ “እግዚአብሔር ሆይ፤ ሕዝብህን አድን፤ርስትህን በአሕዛብ መካከል መተረቻ፣መሣቂያና መሣለቂያም አታድርግ፤ለምንስ በሕዝቦች መካከል፣‘አምላካቸው ወዴት ነው?’ ይበሉን።”

18. እነሆ፤ እግዚአብሔር ስለ ምድሩ ይቀናል፤ስለ ሕዝቡም ይራራል።

19. እግዚአብሔርም እንዲህ ሲል ይመልስላቸዋል፤“እህል፣ አዲስ የወይን ጠጅና ዘይት፣እስክትጠግቡ ድረስ እሰጣችኋለሁ፤የሕዝቦች መዘባበቻ አላደርጋችሁም።

20. “የሰሜንን ሰራዊት ከእናንተ አርቃለሁ፤ፊቱን ወደ ምሥራቁ ባሕር፣ጀርባውንም ወደ ምዕራቡ ባሕር በማድረግ፣ወደ ደረቀውና ወደ ባድማው ምድር እገፋዋለሁ፤ግማቱ ይወጣል፤ክርፋቱም ይነሣል።”በእርግጥ እርሱ ታላቅ ነገር አድርጎአል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኢዩኤል 2