ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ኢሳይያስ 36:1-17 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ንጉሥ ሕዝቅያስ በነገሠ በዐሥራ አራተኛው ዓመት፣ የአሦር ንጉሥ ሰናክሬም የተመሸጉትን የይሁዳ ከተሞች ሁሉ አጥቅቶ ያዛቸው።

2. የአሦርም ንጉሥ የጦር አዛዡን ከብዙ ሰራዊት ጋር ከለኪሶ፣ ንጉሡ ሕዝቅያስ ወዳለበት፣ ወደ ኢየሩሳሌም ላከው። የጦር አዛዡም ወደ ልብስ አጣቢው ዕርሻ በሚወስደው መንገድ፣ በላይኛው ኵሬ ቦይ አጠገብ ደርሶ ቆመ፤

3. የቤተ መንግሥቱ አስተዳዳሪ፣ የኬልቅያስ ልጅ ኤልያቄም፣ ጸሓፊው ሳምናስ፣ ታሪክ መዝጋቢውም የአሳፍ ልጅ ዮአስ ወደ እርሱ ወጡ።

4. የጦር አዛዡም እንዲህ አላቸው፤ “ለሕዝቅያስ እንዲህ ብላችሁ ንገሩት፤“ ‘ታላቁ ንጉሥ የአሦር ንጉሥ እንዲህ ይላል፤ እስከዚህ የተማመንህበት ነገር ምንድን ነው?

5. የጦር ስልትና ጠንካራ ሰራዊት አለኝ ትላለህ፤ ነገር ግን ፍሬ ቢስ ቃል ብቻ ትናገራለህ። ለመሆኑ፣ በእኔ ላይ ያመፅኸው በማን ተማምነህ ነው?

6. እነሆ፤ ሰው ሲመረ ኰዘው እጅ ወግቶ በሚያቈስለው፣ በተሰነጠቀ ሸምበቆ በግብፅ ተማምነሃል፤ የግብፅ ንጉሥ፣ ፈርዖንም ለሚታመኑበት ሁሉ እንዲሁ ነው።

7. ደግሞም፣ “በአምላካችን በእግዚአብሔር እንታመናለን” የምትለኝ ከሆነ፣ የእርሱንማ ማምለኪያ ኰረብቶችና መሠዊያዎች ሕዝቅያስ አፍርሶበት ለይሁዳና ለኢየሩሳሌም፣ “እናንተ መስገድ ያለባችሁ እንዲህ ባለው በአንዱ መሠዊያ ፊት ብቻ ነው” ብሎ የለምን?

8. “ ‘አሁን፣ ናና፣ ከጌታዬ ከአሦር ንጉሥ ጋር ተደራደር፤ የሚቀመጡባቸው ሰዎች ካሉህ፣ ሁለት ሺህ ፈረሶች እሰጥሃለሁ።

9. እንግዲህ በግብፅ ሠረገሎችና ፈረሰኞች የምትተማመን ከሆነ፣ ከጌታዬ መኰንንኖች አንዱን ዝቅተኛ መኰንን እንዴት መመለስ ይቻልሃል?

10. ደግሞስ ይህን ምድር ለማጥቃትና ለማጥፋት የመጣሁት ያለ እግዚአብሔር ትእዛዝ ይመስልሃልን? እግዚአብሔር ራሱ በዚህ አገር ላይ ዘምቼ እንዳጠፋው ነግሮኛል።’ ”

11. ኤልያቄምና ሳምናስ እንዲሁም ዮአስ የጦር አዛዡን፣ “እባክህ በምናውቀው በሶርያ ቋንቋ ለባሪያዎችህ ተናገረን፤ በቅጥሩ ላይ ያለው ሕዝብ በሚያውቀው በዕብራይስጥ ቋንቋ አትናገረን” አሉት።

12. ነገር ግን የጦር አዛዡ መልሶ፣ “ጌታዬ እነዚህን ነገሮች እንድናገር የላከኝ ለጌታህና ለአንተ ብቻ ነበርን? እንደ እናንተ የራሳቸውን ኩስ ለመብላትና ሽንታቸውንም ለመጠጣት በቅጥሩ ላይ ለተቀመጡት ሰዎችም አይደለምን?” አላቸው።

13. የጦር አዛዡም ቆሞ በዕብራይስጥ ቋንቋ በታላቅ ድምፅ እንዲህ አለ፤ “የታላቁን ንጉሥ፣ የአሦርን ንጉሥ ቃል ስሙ።

14. ንጉሡ እንዲህ ይላል፤ ‘ሕዝቅያስ አያታልላችሁ፤ እርሱ ሊያድናችሁም አይችልም።

15. “እግዚአብሔር በርግጥ ያድነናል፤ ይህች ከተማ ለአሦር አትሰጥም’ እያለ ሕዝቅያስ በእግዚአብሔር እንድትታመኑ አያድርጋችሁ።’

16. “ሕዝቅያስን አትስሙ። የአሦር ንጉሥ እንዲህ ይላችኋል፤ ‘ከእኔ ጋር ተስማሙ፤ ወደ እኔም ውጡ። ከዚያም እያንዳንዳችሁ ከወይናችሁና ከበለሳችሁ ትበላላችሁ፤ ከጒድጓዳችሁም ውሃ ትጠጣላችሁ፤

17. ይኸውም መጥቼ የእህልና የአዲስ ወይን ጠጅ ምድር ወደሆነችው፣ የእንጀራና የወይን ምድር ወደሆነችው፣ ምድራችሁን ወደ ምትመስል አገር እስካፈልሳችሁ ድረስ ነው።’

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ኢሳይያስ 36