ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

አስቴር 7:1-7 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ስለዚህ ንጉሡና ሐማ ከንግሥት አስቴር ጋር ለመጋበዝ ሄዱ፤

2. በሁለተኛውም ቀን የወይን ጠጅ እየጠጡ ሳለ፣ ንጉሡ እንደ ገና፣ “ንግሥት አስቴር ሆይ፤ የምትለምኚው ምንድን ነው? ይሰጥሻል፤ የምትጠይቂውስ ምንድን ነው? እስከ መንግሥቴ እኩሌታ እንኳ ቢሆን ይደረግልሻል” አላት።

3. ከዚያም ንግሥት አስቴር እንዲህ ስትል መለሰች፤ “ንጉሥ ሆይ፤ በፊትህ ሞገስ አግኝቼና ግርማዊነትህን ደስ የሚያሰኝ ከሆነ፣ ሕይወቴን ታደጋት፤ ልመናዬ ይህ ነው፤ ሕዝቤን አትርፍ፤ ጥያቄዬም ይኸው ነው።

4. እኔና ሕዝቤ ለጥፋት፣ ለዕርድና ለመደምሰስ ተሸጠናልና። ወንዶችና ሴቶች ባሮች ለመሆን የተሸጥን ቢሆን ኖሮ፣ ዝም ባልሁ ነበር፤ ምክንያቱም እንዲህ ያለው ጭንቀት ንጉሡን ለማስቸገር የሚበቃ አይደለም።”

5. ንጉሥ ጠረክሲስም ንግሥት አስቴርን፣ “ለመሆኑ እርሱ ማን ነው? እንዲህ ያለውን ነገር ለማድረግ እስከዚህ የደፈረውስ ሰው የታለ?” ሲል ጠየቀ።

6. አስቴርም፣ “ያ ባላጋራና ጠላት ይህ ክፉው ሐማ ነው” አለች።ከዚያም ሐማ በንጉሡና በንግሥቲቱ ፊት እጅግ ደነገጠ።

7. ንጉሡ ከተቀመጠበት በቊጣ ተነሣ፤ የወይን ጠጁንም ትቶ ወደ ቤተ መንግሥቱ የአትክልት ቦታ ሄደ። ሐማ ግን ንጉሡ ሊያጠፋው ቈርጦ መነሣቱን ስላወቀ፣ ንግሥት አስቴር ሕይወቱን እንድታተርፍለት ለመማጠን በዚያው ቀረ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ አስቴር 7