ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

አስቴር 5 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

አስቴር ለንጉሡ ያቀረበችው ልመና

1. በሦስተኛው ቀን አስቴር የክብር ልብሷን ለብሳ በንጉሡ አዳራሽ ፊት ለፊት ባለው በቤተ መንግሥቱ ውስጠኛ አደባባይ ገብታ ቆመች። ንጉሡም አዳራሹ ውስጥ በመግቢያው ትይዩ በዙፋኑ ላይ ተቀምጦ ነበር።

2. ንግሥት አስቴር በአደባባዩ ላይ ቆማ ሲያያት ደስ አለው፤ በእጁ የያዘውን የወርቅ ዘንግ ዘረጋላት፤ አስቴርም ቀረብ ብላ የዘንጉን ጫፍ ነካች።

3. ከዚያም ንጉሡ፣ “ንግሥት አስቴር ሆይ፤ ለምን መጣሽ? ከእኔ የምትፈልጊውስ ምንድን ነው? እስከ መንግሥቴ እኩሌታ እንኳ ቢሆን ይሰጥሻል” አላት።

4. አስቴርም መልሳ፣ “ንጉሡን ደስ የሚያሰኘው ቢሆን፣ ባዘጋጀሁለት ግብዣ ላይ ንጉሡ ዛሬ ከሐማ ጋር ይገኝልኝ” አለች።

5. ንጉሡም፣ “አስቴር ያለችውን እንድንፈጽም፣ ሐማን በፍጥነት ጥሩት” አለ። ስለዚህ ንጉሡና ሐማ አስቴር ወዳዘጋጀችው ግብዣ ሄዱ።

6. የወይን ጠጅ እየጠጡ ሳለ ንጉሡ ዳግመኛ አስቴርን፣ “እስቲ የምትፈልጊው ምንድን ነው? ይሰጥሻል፤ ደግሞስ የምትጠዪቂው ምንድን ነው? እስከ መንግሥቴ እኩሌታ እንኳ ቢሆን ይፈቀድልሻል” አላት።

7. አስቴርም እንዲህ ስትል መለሰች፤ “ልመናዬም፣ ጥያቄዬም ይህ ነው፤

8. በንጉሡ ዘንድ ሞገስ ካገኘሁና የምፈልገውን ሊሰጠኝና ልመናዬንም ሊፈጽምልኝ ንጉሡን ደስ ካሰኘው፣ ንጉሡና ሐማ በማዘጋጅላቸው ግብዣ ላይ ነገ ይገኙልኝ። ከዚያም እኔ ለንጉሡ ጥያቄ መልስ እሰጣለሁ።”

ሐማ በመርዶክዮስ ላይ ያወረደው ቊጣ

9. ሐማ በዚያን ቀን ደስ ብሎትና መንፈሱ ረክቶ ወጣ፤ ነገር ግን መርዶክዮስን በንጉሡ በር ላይ ሲያየው ከተቀመጠበት አለመነሣቱንና በፊቱም አለመንቀጥቀጡን ሲመለከት፣ ቊጣው በመርዶክዮስ ላይ ነደደ።

10. ሐማ ግን እንደምንም ራሱን ተቈጣጥሮ ወደ ቤቱ ሄደ።ወዳጆቹንና ሚስቱን ዞሳራን አስጠርቶ በአንድነት ከሰበሰባቸው በኋላ፣

11. ሐማ ስለ ሀብቱ ታላቅነት፣ ስለ ልጆቹ ብዛት እንዲሁም ንጉሡ የቱን ያህል እንዳከበረው፣ ከሌሎቹም መኳንንትና ሹማምት ይበልጥ እንዴት ከፍ ከፍ እንዳደረገው እያጋነነ ነገራቸው።

12. ሐማም፣ “ምን ይኽ ብቻ” አለ፤ “ንግሥት አስቴር ባዘጋጀችው ግብዣ ላይ ከንጉሡ ጋር እንድገኝ የጋበዘችው ሰው አንድ እኔ ብቻ ነኝ፤ ነገም ከንጉሡ ጋር ጋብዛኛለች።

13. ነገር ግን አይሁዳዊው መርዶክዮስ በንጉሡ በር ላይ ተቀምጦ ካየሁት ይህ ሁሉ እኔን ደስ አያሰኘኝም።”

14. ሚስቱ ዞሳራና ወዳጆቹ በሙሉ፣ “ቁመቱ አምሳ ክንድ የሆነ መስቀያ አስተክልና መርዶክዮስ እንዲሰቀልበት በጠዋት ለንጉሡ ንገረው፤ ከዚያም ደስ ብሎህ ከንጉሡ ጋር ወደ ግብዣው ግባ” አሉት። ይህም ሐሳብ ሐማን እጅግ ደስ አሰኘው፤ መስቀያውንም አስተከለ።