ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

አስቴር 3:1-15 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ከዚህም ነገር በኋላ ንጉሥ ጠረክሲስ የአጋጋዊውን የሐመዳቱን ልጅ ሐማን ከፍ ከፍ አደረገው፤ ከሌሎቹም መኳንንት ሁሉ ከፍተኛውን ሥልጣን በመስጠት አከበረው።

2. ንጉሡ ስለ እርሱ ይህ እንዲደረግለት አዞ ስለ ነበር፣ በንጉሡ በር ያሉት የመንግሥቱ ሹማምት ሁሉ ለሐማ ተንበርክከው እጅ በመንሣት አክብሮታቸውን ይገልጡለት ነበር። መርዶክዮስ ግን ወድቆ አልሰገደለትም፤ አክብሮትም አላሳየውም።

3. ታዲያ በንጉሡ በር ያሉት የንጉሡ አገልጋዮች መርዶክዮስን፣ “የንጉሡን ትእዛዝ ለምን ትተላለፋለህ?” ሲሉ ጠየቁት።

4. ይህንንም በየቀኑ ይነግሩት ነበር፤ እርሱ ግን አልተቀበላቸውም። አይሁዳዊ መሆኑን ነግሮአቸው ስለ ነበር፣ የመርዶክዮስ ባሕርይ እስከ መቼ ሊቀጥል እንደሚችል ለማየት ሲሉ ይህንኑ ለሐማ ነገሩት።

5. ሐማም መርዶክዮስ ወድቆ እንዳልሰገደለትና እንዳላከበረው ሲያይ እጅግ ተቈጣ።

6. ይልቁንም መርዶክዮስ ከእነማን ወገን መሆኑን በተረዳ ጊዜ፣ መርዶክዮስን ብቻ መግደል እንደ ኢምንት ቈጠረው፤ ስለዚህ ሐማ በመላው የጠረክሲስ መንግሥት ውስጥ የሚገኙትንና የመርዶክዮስ ወገን የሆኑትን አይሁድ ሁሉ ለማጥፋት ዘዴ ፈለገ።

7. ንጉሥ ጠረክሲስ በነገሠ በዐሥራ ሁለተኛው ዓመት ኒሳን በተባለው በመጀመሪያው ወር፣ ቀኑንና ወሩን ለመለየት ፉር የተባለ ዕጣ ሐማ ባለበት ጣሉ፤ ዕጣውም አዳር በተባለው በዐሥራ ሁለተኛው ወር ላይ ወደቀ።

8. ከዚያም ሐማ ንጉሥ ጠረክሲስን እንዲህ አለው፤ “በአሕዛብ መካከል በመንግሥትህ አውራጃዎች ሁሉ ተሠራጭቶና ተበታትኖ የሚኖር አንድ ሕዝብ አለ፤ ይህም ሕዝብ ከሌሎች ሕዝቦች ሁሉ የተለየ ልማድ ያለውና የንጉሡንም ሕግ የማይታዘዝ ነው፤ ታዲያ ይህን ሕዝብ ዝም ማለቱ ለንጉሡ አይበጅም።

9. ነገሩ ንጉሡን ደስ የሚያሰኘው ከሆነ፣ እነርሱን ለማጥፋት ዐዋጅ ይውጣ፤ እኔም ይህን ተግባር ለሚፈጽሙ ሰዎች የሚውል ዐሥር ሺህ መክሊት ብር ወደ መንግሥት ግምጃ ቤት አስገባለሁ።”

10. ስለዚህ ንጉሡ የቀለበት ማኅተሙን ከጣቱ አውልቆ የአይሁድ ጠላት ለሆነው ለአጋጋዊው ለሐማዳቱ ልጅ ለሐማ ሰጠው።

11. ንጉሡም ሐማን፣ “ገንዘቡን እዚያው ያዘው፤ ሕዝቡንም እንዳሻህ አድርገው” አለው።

12. ከዚያም በመጀመሪያው ወር ዐሥራ ሦስተኛው ቀን የንጉሡ ጸሓፊዎች ተጠሩ። እነርሱም የሐማን ትእዛዝ በሙሉ በየአውራጃው ፊደልና በየሕዝቡ ቋንቋ፣ ለንጉሡ እንደራሴዎች፣ ለልዩ ልዩ አውራጃ ገዦችና ለልዩ ልዩ ሕዝቦች መኳንንት ጻፉ። ይህም የተጻፈው በራሱ በንጉሡ ጠረክሲስ ስም ሲሆን፣ የታተመውም በራሱ ማኅተም ነበር።

13. አዳር በተባለው በዐሥራ ሁለተኛው ወር፣ በዐሥራ ሦስተኛው ቀን ወጣት፣ ሽማግሌ፣ ሴትና ሕፃን ሳይባል አይሁድ ሁሉ በዚያኑ ዕለት እንዲጠፉ፣ እንዲገደሉና እንዲደመሰሱ፣ ሀብታቸውም እንዲዘረፍ ደብዳቤ ለንጉሡ አውራጃዎች ሁሉ በመልእክተኞች እጅ ተላከ።

14. ለእያንዳንዱም አውራጃ ሕዝብ እንዲታወቅ፣ እነርሱም ለዚያ ቀን ዝግጁ እንዲሆኑ፣ የዋናው ዐዋጅ ቅጅ ሕግ እንዲወጣና ወደ እያንዳንዱም አውራጃ እንዲላክ ተደረገ።

15. መልእክተኞቹ በንጉሡ ትእዛዝ ተቻኵለው ወጡ፤ ዐዋጁም በሱሳ ግንብ ተላለፈ። ንጉሡና ሐማ ለመጠጣት ተቀመጡ፤ የሱሳ ከተማ ግን ግራ ተጋብታ ነበር።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ አስቴር 3