ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ምሳሌ 22:3-15 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

3. አስተዋይ ሰው አደጋ ሲያይ መጠጊያ ይሻል፤ብስለት የጐደለው ግን በዚያው ይቀጥላል፤ መከራም ያገኘዋል።

4. ትሕትናና እግዚአብሔርን መፍራት፣ሀብትን፣ ክብርንና ሕይወትን ያስገኛል።

5. በክፉዎች መንገድ ላይ እሾህና ወጥመድ አለ፤ነፍሱን የሚጠብቅ ግን ከእነዚህ ይርቃል።

6. ልጅን የሚሄድበትን መንገድ አስተምረው፤በሚሸመግልበት ጊዜ ከዚያ ፈቀቅ አይልም።

7. ባለጠጋ ድኻን ይገዛል፤ተበዳሪም የአበዳሪ ባሪያ ነው።

8. ክፋትን የሚዘራ መከራን ያጭዳል፤የቊጣውም በትር ይጠፋል።

9. ቸር ሰው ራሱ ይባረካል፤ምግቡን ከድኾች ጋር ይካፈላልና።

10. ፌዘኛን አስወጣው፤ ጠብ ይወገዳል፤ጥልና ስድብም ያከትማል።

11. የልብ ንጽሕናን ለሚወድና ንግግሩም ሞገስ ላለው ሰው፣ንጉሥ ወዳጁ ይሆናል።

12. የእግዚአብሔር ዐይኖች ዕውቀትን ይጠብቃሉ፤የማይታመኑትን ሰዎች ቃል ግን እርሱ ከንቱ ያደርጋል።

13. ሰነፍ፣ “አንበሳ ውጪ አለ፤መንገድ ላይ እገደላለሁ” ይላል።

14. የአመንዝራ ሴት አፍ ጥልቅ ጒድጓድ ነው፤ እግዚአብሔር የተቈጣውም ይገባበታል።

15. ሞኝነት በሕፃን ልብ ታስሮአል፤የተግሣጽ በትር ግን ከእርሱ ያርቅለታል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ምሳሌ 22