ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ምሳሌ 2:1-16 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ልጄ ሆይ፤ ቃሌን ብትቀበል፣ትእዛዜንም በልብህ ብታኖር፣

2. ጆሮህን ወደ ጥበብ ብታቀና፣ልብህንም ወደ ማስተዋል ብትመልስ፣

3. እንዲሁም የመለየት ጥበብን ብትማጠን፣ድምፅህን ከፍ አድርገህ ማስተዋልን ብትጣራ፣

4. እርሷንም እንደ ብር ብትፈልጋት፣እንደ ተሸሸገ ሀብት አጥብቀህ ብትሻት፣

5. በዚያን ጊዜ ፈሪሀ እግዚአብሔርን ትረዳለህ፤አምላክንም ማወቅ ታገኛለህ።

6. እግዚአብሔር ጥበብን ይሰጣልና፤ከአንደበቱም ዕውቀትና ማስተዋል ይወጣል።

7. እርሱ ለቅኖች ድልን ያከማቻል፤ያለ ነቀፋ ለሚሄዱትም ጋሻ ይሆናቸዋል፤

8. የፍትሕን መንገድ ይጠብቃል፤የታማኞቹንም አካሄድ ያጸናል።

9. በዚያን ጊዜ ጽድቅን፣ ፍትሕን፣ ሚዛናዊነትን፣መልካሙንም መንገድ ሁሉ ትገነዘባለህ፤

10. ጥበብ ልብህ ውስጥ ትገባለችና፤ዕውቀትም ነፍስህን ደስ ታሰኛለች፤

11. የመለየት ችሎታ ይጋርድሃል፤ማስተዋልም ይጠብቅሃል።

12. ጥበብ ንግግራቸው ጠማማ ከሆነ ሰዎች፣ከክፉዎችም መንገድ ታድንሃለች፤

13. እነዚህም በጨለማ መንገድ ለመሄድ፣ቀናውን ጐዳና የሚተዉ ናቸው፤

14. ክፉ በመሥራት ደስ የሚላቸው፣በክፋት ጐዳና ሐሤት የሚያደርጉ፣

15. መንገዳቸው ጠማማ፣በአካሄዳቸው ጠመዝማዞች ናቸው።

16. ከአመንዝራ ሴትም ትጠብቅሃለች፤በአንደበቷም ከምታታልል ዘልዛላ ታድንሃለች፤

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ምሳሌ 2