ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ማሕልየ መሓልይ 2:1-14 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. እኔ የሳሮን ጽጌረዳ፣የሸለቆም አበባ ነኝ።

2. በእሾኽ መካከል እንዳለ ውብ አበባ፣ውዴም በቈነጃጅት መካከል እንዲሁ ናት።

3. በዱር ዛፎች መካከል እንዳለ እንኰይ፣ውዴም በጐልማሶች መካከል እንዲሁ ነው፤በጥላው ሥር መቀመጥ ደስ ያሰኛል፤የፍሬውም ጣፋጭነት ያረካኛል።

4. ወደ ግብዣው አዳራሽ ወሰደኝ፤በእኔ ላይ ያለው ዐላማው ፍቅር ነው።

5. በዘቢብ አበረታቱኝ፤በእንኰይም አስደስቱኝ፤በፍቅሩ ተይዤ ታምሜአለሁና።

6. ግራ እጁን ተንተርሻለሁ፤ቀኝ እጁም ዐቅፎኛል።

7. እናንት የኢየሩሳሌም ቈነጃጅት፣ራሱ እስኪፈልግ ድረስ፣ፍቅርን እንዳታስነሡት ወይም እንዳትቀሰቅሱት፣በሚዳቋና በሜዳ ዋልያ አማጥናችኋለሁ።

8. እነሆ፤ የውዴ ድምፅበተራሮች ላይ እየዘለለ፣በኰረብቶችም ላይ እየተወረወረ፣ሲመጣ ይሰማኛል።

9. ውዴ ሚዳቋ ወይም የዋልያ ግልገል ይመስላል፤እነሆ፤ ከቤታችን ግድግዳ ኋላ ቆሞአል፤በመስኮት ትክ ብሎ ወደ ውስጥ ያያል፤በፍርግርጉም እያሾለከ ይመለከታል።

10. ውዴም እንዲህ አለኝ፤“ፍቅሬ ሆይ፤ ተነሺ፤አንቺ የእኔ ቈንጆ፤ ከእኔ ጋር ነዪ።

11. እነሆ! ክረምቱ ዐለፈ፤ዝናሙም አባርቶ አበቃ፤

12. አበቦች በምድር ላይ ታዩ፤የዝማሬ ወቅት መጥቶአል፤የርግቦችም ድምፅ፣በምድራችን ተሰማ።

13. በለስ ፍሬዋን አፈራች፤ያበቡ ወይኖችም መዐዛቸውን ሰጡ፤ፍቅሬ ሆይ፤ ተነሺና ነዪ፤አንቺ የእኔ ቈንጆ፤ ከእኔ ጋር ነዪ።”

14. አንቺ በገደል ዐለት ንቃቃት፣በተራሮችም ባሉ መደበቂያ ስፍራዎች ውስጥ ያለሽ ርግቤ ሆይ!ፊትሽን አሳይኝ፤ድምፅሽንም አሰሚኝ፤ድምፅሽ ጣፋጭ፣መልክሽም ውብ ነውና።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ማሕልየ መሓልይ 2