ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 89:35-49 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

35. አንድ ጊዜ በቅድስናዬ ምያለሁና፣ዳዊትን አልዋሸውም።

36. የዘር ሐረጉ ለዘላለም፣ዙፋኑም በፊቴ እንደ ፀሓይ ጸንቶ ይኖራል፤

37. በሰማይ ታማኝ ምስክር ሆና እንደምትኖረው፣እንደ ጨረቃ እርሱ ለዘላለም ይመሠረታል።” ሴላ

38. አሁን ግን ናቅኸው፤ ጣልኸውም፤የቀባኸውንም እጅግ ተቈጣኸው።

39. ከባሪያህ ጋር የገባኸውን ኪዳን አፈረስህ፤የክብር ዘውዱን ትቢያ ላይ ጥለህ አቃለልኸው።

40. ቅጥሩን ሁሉ አፈራረስህ፤ምሽጉንም ደመሰስህ።

41. ዐላፊ አግዳሚው ሁሉ ዘረፈው፤ለጎረቤቶቹ መዘባበቻ ሆነ።

42. የጠላቶቹን ቀኝ እጅ ከፍ ከፍ አደረግህ፤ባላንጣዎቹም ሁሉ ደስ አላቸው።

43. የሰይፉን ስለት አጠፍህ፤በጦርነትም ጊዜ አልረዳኸውም።

44. ግርማዊነቱን አጠፋህበት፤ዙፋኑንም ከዐፈር ደባለቅኸው።

45. የወጣትነት ዘመኑን አሳጠርኸው፤ዕፍረትንም አከናነብኸው። ሴላ

46. እግዚአብሔር ሆይ፤ ይህ እስከ መቼ ይሆናል? ራስህንስ ለዘላለም ትሰውራለህን?ቍጣህስ እንደ እሳት የሚነደው እስከ መቼ ነው?

47. ዘመኔ ምን ያህል አጭር እንደሆነች አስብ፤የሰውን ልጆች እንዲያው ለከንቱ ፈጠርሃቸው!

48. ሞትን ሳያይ ሕያው ሆኖ የሚቀርሰው አለን?ራሱን ከሲኦል እጅ ማዳን የሚችል ማን ነው? ሴላ

49. ጌታ ሆይ፤ ለዳዊት በታማኝነትህ የማልህለት፣የቀድሞው ምሕረትህ የት አለ?

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 89