ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 45:1-11 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ልቤ መልካም ሐሳብ አፈለቀ፤የተቀኘሁትን ቅኔ ለንጉሥ አሰማለሁ፤አንደበቴም እንደ ባለ ሙያ ጸሓፊ ብርዕ ነው።

2. አንተ ከሰዎች ሁሉ ይልቅ ውብ ነህ፤ከንፈሮችህም የጸጋ ቃል ያፈልቃሉ፤ስለዚህ እግዚአብሔር ለዘላለም ባርኮሃል።

3. ኀያል ሆይ፤ ሰይፍህን በወገብህ ታጠቅ፤ግርማ ሞገስንም ተላበስ።

4. ስለ እውነት፣ ስለ ትሕትና ስለ ጽድቅ፣ሞገስን ተጐናጽፈህ በድል አድራጊነት ገሥግሥ፤ቀኝ እጅህም ድንቅ ተግባር ታሳይ።

5. የሾሉ ፍላጻዎችህ በንጉሥ ጠላቶች ልብ ይሰካሉ፤ሕዝቦችም ከእግርህ በታች ይወድቃሉ።

6. አምላክ ሆይ፤ ዙፋንህ ከዘላለም እስከ ዘላለም ይኖራል፤የመንግሥትህ በትር የቅንነት በትር ናት።

7. ጽድቅን ወደድህ፤ ዐመፃን ጠላህ፤ስለዚህ እግዚአብሔር አምላክህ፣ከጓደኞችህ ይልቅ አንተን የደስታ ዘይት ቀባህ።

8. ልብስህ ሁሉ በከርቤ፣ በአደስና በጥንጁት መዐዛ ያውዳል፤በዝኆን ጥርስ ከተዋቡ ቤተ መንግሥቶችም፣የበገናና የመሰንቆ ድምፅ ደስ ያሰኙሃል።

9. ከተከበሩት ሴቶችህ መካከል የነገሥታት ሴቶች ልጆች ይገኛሉ፤ንግሥቲቱም በኦፊር ወርቅ አጊጣ በቀኝህ ቆማለች።

10. ልጄ ሆይ፤ አድምጪ፤ አስተዉይ፤ ጆሮሽንም አዘንብይ፤ሕዝብሽንና የአባትሽን ቤት እርሺ።

11. ንጉሥ በውበትሽ ተማርኮአል፤ጌታሽ ነውና አክብሪው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 45