ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 42:1-11 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ዋላ የምንጭ ውሃ እንደምትናፍቅ፣አምላክ ሆይ፤ ነፍሴም እንዲሁ አንተን ትናፍቃለች።

2. ነፍሴ አምላክን፣ ሕያው አምላክን ተጠማች፤መቼ ደርሼ ነው የአምላክን ፊት የማየው?

3. ሰዎች ቀኑን ሙሉ፣“አምላክህ የት አለ?” ባሉኝ ቍጥር፣እንባዬ ቀንና ሌሊት፣ምግብ ሆነኝ።

4. ነፍሴ በውስጤ እየፈሰሰች፣እነዚህን ነገሮች አስታወስሁኝ፤ታላቅ ሕዝብ ወደ እግዚአብሔር ቤት እየመራሁ፣በእልልታና በምስጋና መዝሙር፣በአእላፍ ሕዝብ መካከል፣እንዴት ከሕዝቡ ጋር እሄድ እንደ ነበር ትዝ አለኝ።

5. ነፍሴ ሆይ፤ ለምን ትተክዢያለሽ?ለምንስ በውስጤ ትታወኪያለሽ?ተስፋሽን በአምላክ ላይ አድርጊ፤አዳኜና

6. አምላኬን፣ ገና አመሰግነዋለሁና።ነፍሴ በውስጤ ተክዛለች፤ስለዚህ በዮርዳኖስ ምድር፣በአርሞንኤም ከፍታ፣ በሚዛር ተራራ አስብሃለሁ።

7. በፏፏቴህ ማስገምገም፣አንዱ ጥልቅ ሌላውን ጥልቅ ይጣራል፤ማዕበልህና ሞገድህ ሁሉ፣ሙሉ በሙሉ አጥለቀለቀኝ።

8. እግዚአብሔር ምሕረቱን በቀን ያዝዛል፤ዝማሬውም በሌሊት በእኔ ዘንድ አለ፤ይህም ለሕይወቴ አምላክ የማቀርበው ጸሎት ነው።

9. እግዚአብሔር ዐለቴን፣“ለምን ረሳኸኝ?ጠላትስ እያስጨነቀኝ፣ለምን በሐዘን እመላለሳለሁ?” እለዋለሁ።

10. ጠላቶቼ ቀኑን ሙሉ፣“አምላክህ የት አለ?” እያሉ፣በነገር ጠዘጠዙኝ፣ዐጥንቴም ደቀቀ።

11. ነፍሴ ሆይ፤ ለምን ትተክዢያለሽ?ለምንስ በውስጤ ትታወኪያለሽ?ተስፋሽን በአምላክ ላይ አድርጊ፣አዳኜና አምላኬን፣ገና አመሰግነዋለሁ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 42