ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 147:1-15 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. ሃሌ ሉያ።አምላካችንን በመዝሙር ማወደስ እንዴት መልካም ነው፤እርሱን ማመስገን ደስ ያሰኛል፤ ይህ ተገቢም ነው።

2. እግዚአብሔር ኢየሩሳሌምን መልሶ ይሠራታል፤ከእስራኤል የተበተኑትን ይሰበስባል።

3. ልባቸው የተሰበረውን ይፈውሳል፤ቍስላቸውንም ይጠግናል።

4. የከዋክብትን ብዛት ያውቃል፤እያንዳንዱንም በስሙ ይጠራዋል።

5. ጌታችን ታላቅ ነው፤ እጅግ ኀያልም ነው፤ለጥበቡም ወሰን የለውም።

6. እግዚአብሔር ትሑታንን ከፍ ያደርጋል፤ክፉዎችን ግን ወደ ምድር ይጥላል።

7. ለእግዚአብሔር በምስጋና ዘምሩ፤ለአምላካችንም በመሰንቆ ምስጋና አቅርቡ።

8. ሰማይን በደመናት የሚሸፍን እርሱ ነው፤ለምድርም ዝናብን ይሰጣል፤በተራሮችም ላይ ሣር ያበቅላል።

9. ለእንስሳት ምግባቸውን፣የቍራ ጫጩቶችም ሲንጫጩ የሚበሉትን ይሰጣቸዋል።

10. እርሱ በፈረስ ኀይል አይደሰትም፤በሯጭም ብርታት ላይ ደስታውን አያደርግም።

11. ነገር ግን እግዚአብሔር በሚፈሩት፣በምሕረቱ በሚታመኑትም ይደሰታል።

12. ኢየሩሳሌም ሆይ፤ እግዚአብሔርን አመስግኚ፤ጽዮን ሆይ፤ አምላክሽን አወድሺ፤

13. እርሱ የደጆችሽን መወርወሪያ አጽንቶአልና፤ልጆችሽንም በውስጥሽ ባርኮአል።

14. በድንበርሽ ውስጥ ሰላም ያሰፍናል፤ማለፊያ ስንዴም ያጠግብሻል።

15. ትእዛዙን ወደ ምድር ይልካል፤ቃሉም እጅግ በፍጥነት ይሮጣል።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 147