ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መዝሙር 145:1-13 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. አምላኬና ንጉሤ ሆይ፤ ከፍ ከፍ አደርግሃለሁ፤ስምህን ከዘላለም እስከ ዘላለም እባርካለሁ።

2. በየቀኑ እባርክሃለሁ፤ስምህንም ከዘላለም እስከ ዘላለም አመሰግናለሁ።

3. እግዚአብሔር ታላቅ ነው፤ እጅግ ሊመሰገንም ይገባዋል፤ታላቅነቱም አይመረመርም።

4. ሥራህን አንዱ ትውልድ ለሌላው ትውልድ ያስተጋባል፤ብርቱ ሥራህን ያውጃል።

5. ስለ ግርማህ ውበትና ክብር ይናገራሉ፤ስለ ድንቅ ሥራህም ያወራሉ።

6. ስለ ድንቅ ሥራህ ብርታት ይነጋገራሉ፤እኔም ስለ ታላቅነትህ ዐውጃለሁ።

7. የበጎነትህን ብዛት በደስታ ያወሳሉ፤ስለ ጽድቅህም በእልልታ ይዘምራሉ።

8. እግዚአብሔር ቸር ነው፤ ርኅሩኅም ነው፤ለቍጣ የዘገየ፣ ምሕረቱ የበዛ።

9. እግዚአብሔር ለሁሉ ቸር ነው፤ምሕረቱም በፍጥረቱ ሁሉ ላይ ነው።

10. እግዚአብሔር ሆይ፤ ፍጥረትህ ሁሉ ያመሰግንሃል፤ቅዱሳንህም ይባርኩሃል።

11. ስለ መንግሥትህ ክብር ይናገራሉ፤ስለ ኀይልህም ይነጋገራሉ፤

12. በዚህም ብርቱ ሥራህን፣የመንግሥትህንም ግርማ ክብር ያስታውቃሉ።

13. መንግሥትህ የዘላለም መንግሥት ናት፤ግዛትህም ለትውልድ ሁሉ ጸንቶ ይኖራል። እግዚአብሔር ቃሉን ሁሉ ይጠብቃል፤በሥራውም ሁሉ ቸር ነው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መዝሙር 145