ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መክብብ 7:1-14 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. መልካም ስም ከመልካም ሽቱ ይበልጣል፤ከልደትም ቀን የሞት ቀን ይሻላል።

2. ወደ ግብዣ ቤት ከመሄድ፣ወደ ሐዘን ቤት መሄድ ይሻላል፤ሞት የሰው ሁሉ ፍጻሜ ነውና፤ሕያው የሆነም ይህን ልብ ማለት ይገባዋል።

3. ሐዘን ከሣቅ ይሻላል፤ያዘነ ፊት ለልብ መልካም ነውና።

4. የጠቢባን ልብ በሐዘን ቤት ነው፤የሞኞች ልብ ግን በደስታ ቤት ነው።

5. የሞኞችን መዝሙር ከመስማት፣የጠቢባንን ሰዎች ተግሣጽ መስማት ይሻላል።

6. የሰነፎች ሣቅ፣ከድስት ሥር እንደሚንጣጣ የእሾኽ ማገዶ ነው፤ይህም ደግሞ ከንቱ ነው።

7. ግፍ ጠቢብን ሞኝ ያደርጋል፤ጒቦም ልብን ያበላሻል።

8. የአንድ ነገር ፍጻሜ ከጅማሬው ይሻላል፤ትዕግሥተኛም ከትዕቢተኛ ይሻላል፤

9. የሞኞች ቊጣ በዕቅፋቸው ውስጥ ስለ ሆነ፣በመንፈስህ ለቊጣ አትቸኵል።

10. አንተም፣ “ከእነዚህ ቀናት የቀድሞዎቹ ለምን ተሻሉ?” አትበል፤እንዲህ ያሉትን ጥያቄዎች መጠየቅ ጠቢብነት አይደለምና።

11. ጥበብ እንደ ርስት መልካም ነገር ነው፤ጠቃሚነቱም ፀሓይን ለሚያዩ ሰዎች ነው።

12. ገንዘብ ጥላ ከለላ እንደሆነ ሁሉ፣ጥበብም ጥላ ከለላ ነው፤የዕውቀት ብልጫዋ ግን፣ጥበብ የባለቤቷን ሕይወት መጠበቋ ነው።

13. እግዚአብሔር ያደረገውን ተመልከት፤እርሱ ያጣመመውን፣ማን ሊያቃናው ይችላል?

14. ጊዜው መልካም ሲሆን፣ ደስ ይበልህ፤ጊዜው ክፉ ሲሆን ግን ይህን አስብ፤እግዚአብሔር አንዱን እንዳደረገ፣ሌላውንም አድርጎአል፤ስለዚህ ሰው ስለ ወደ ፊት ሁኔታው፣ምንም ሊያውቅ አይችልም።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መክብብ 7