ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መክብብ 3:12-21 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

12. ለሰዎች፣ በሕይወት እያሉ ደስ ከመሰኘትና መልካምን ነገር ከማድረግ የተሻለ ነገር እንደሌለ ዐወቅሁ።

13. ሰው ሁሉ ይበላና ይጠጣ ዘንድ፣ በሚደክምበትም ሁሉ ርካታን ያገኝ ዘንድ ይህ የእግዚአብሔር ችሮታ ነው።

14. እግዚአብሔር ያደረገው ሁሉ ለዘላለም እንደሚኖር ዐውቃለሁ፤ በእርሱ ላይ ምንም አይጨመርም፤ ከእርሱም ምንም አይቀነስም፤ ሰዎች ያከብሩት ዘንድ ይህን አደረገ።

15. አሁን ያለው ከዚህ በፊት የነበረው ነው፤ወደ ፊት የሚሆነውም ቀድሞ የነበረ ነው፤እግዚአብሔርም ያለፈውን መልሶ ይሻዋል።

16. ከፀሓይ በታችም ሌላ ነገር አየሁ፤በፍርድ ቦታ ዐመፅ ነበር፤በፍትሕ ቦታ ግፍ ነበር።

17. እኔም በልቤ“ለማንኛውም ድርጊት፣ለማንኛውም ተግባር ጊዜ ስላለው፣እግዚአብሔር ጻድቁንና ኀጢአተኛውን ወደ ፍርድ ያመጣቸዋል”ብዬ አሰብሁ።

18. እንዲህም ብዬ አሰብሁ፤ “ሰዎች፣ እንደ እንስሳት መሆናቸውን ያዩ ዘንድ እግዚአብሔር ይፈትናቸዋል።

19. የሰው ዕድል ፈንታ እንደ እንስሳት ነው፤ ሁለቱም ዕጣ ፈንታቸው አንድ ነው፤ አንዱ እንደሚሞት፣ ሌላውም እንዲሁ ይሞታል። ሁሉ አንድ ዐይነት እስትንፋስ አላቸው፤ ሰውም ከእንስሳ ብልጫ የለውም፤ ሁሉም ከንቱ ነው።

20. ሁሉም ወደ አንድ ቦታ ይሄዳሉ፤ ሁሉም ከዐፈር እንደሆኑ፣ ተመልሰው ወደ ዐፈር ይሄዳሉ።

21. የሰው መንፈስ ወደ ላይ መውጣቱን፣ የእንስሳ እስትንፋስ ደግሞ ወደ ታች ወደ ምድር መውረዱን ማን ያውቃል?”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መክብብ 3