ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

መሳፍንት 3:19-31 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

19. እርሱ ራሱ ግን ጌልጌላ አጠገብ ድንጋዮች ተጠርበው ከሚወጡበት አካባቢ ሲደርስ ወደ ኋላ በመመለስ ወደ ንጉሡ ሄዶ፣ “ንጉሥ ሆይ፤ በምስጢር የምነግርህ ነገር አለኝ” አለው።ንጉሡም፣ “ጸጥታ” ሲል፤ አጠገቡ የነበሩት አገልጋዮች በሙሉ ትተውት ወጡ።

20. ንጉሡ ሰገነት ላይ ባለው ነፋሻ ዕልፍኝ ውስጥ ብቻውን ተቀምጦ ሳለ ናዖድ ቀረብ ብሎ፣ “ከእግዚአብሔር ዘንድ ለአንተ ያመጣሁት መልእክት አለኝ” አለው፤ ንጉሡም ከዙፋኑ ተነሣ።

21. ናዖድ ግራ እጁን ሰደድ በማድረግ ሰይፉን ከደበቀበት ከቀኝ ጭኑ መዝዞ በንጉሡ ሆድ ሻጠው።

22. እጀታው ሳይቀር ሰይፉ እንዳለ ሆዱ ውስጥ ገባ፤ ስለቱም በጀርባው ወጣ፤ ሞራም ስለቱን ሸፈነው፤ ናዖድ ሰይፉን ስላልነቀለው አንጀቱ ተዘረገፈ።

23. ከዚያም በኋላ ናዖድ በዕልፍኙ መግቢያ ወጣ፤ የዕልፍኙንም በር በንጉሡ ላይ ዘግቶ ቈለፈው።

24. ናዖድ ከሄደ በኋላ፣ የንጉሡ አገልጋዮች ሲመጡ፣ የዕልፍኙ በር ተቈልፎ አገኙት፤ እነርሱም፣ “በውስጠኛው ክፍል እየተጸዳዳ ይሆናል” አሉ፤

25. እስኪደክማቸውም ድረስ ጠበቁ፤ ነገር ግን ንጉሡ የእልፍኙን በሮች ባለመክፈቱ ቍልፍ ወስደው ከፈቱ፤ በዚያም ጌታቸው ሞቶ፣ በወለሉም ላይ ተዘርግቶ አገኙት።

26. የንጉሡ አገልጋዮች በዕልፍኙ በር ላይ ቆመው ሲጠባበቁ ናዖድ ርቆ ሄደ፤ ድንጋዮች ተጠርበው በሚወጡበት በኩል ወደ ሴርታይም አመለጠ።

27. እዚያም እንደ ደረሰ፣ በኰረብታማው በኤፍሬም ምድር ቀንደ መለከቱን ነፋ፤ እስራኤላውያንም በእርሱ መሪነት ከኰረብታው ላይ አብረውት ወረዱ።

28. እርሱም፣ “ጠላታችሁን ሞዓብን እግዚአብሔር በእጃችሁ አሳልፎ ስለ ሰጣችሁ ተከተሉኝ” በማለት አዘዛቸው፤ እነርሱም ተከትለውት ወረዱ፤ ከዚያም ከዮርዳኖስ ወደ ሞዓብ የሚያሻግሩትን መልካዎች በመያዝ አንድም ሰው እንዳያልፍ ከለከሉ።

29. በዚያን ጊዜ ብርቱና ኀይለኛ የሆኑ ዐሥር ሺህ ሞዓባውያንን ገደሉ፤ አንድም ሰው አላመለጠም።

30. በዚያን ቀን ሞዓብ በእስራኤል ድል ሆነች፤ ምድሪቱም ለሰማንያ ዓመት ሰላም አገኘች።

31. ከናዖድ በኋላ ስድስት መቶ ፍልስጥኤማውያንን በበሬ መንጃ የገደለው የዓናት ልጅ ሰሜጋር ተነሣ፤ እርሱም እንደዚሁ ደግሞ እስራኤልን አዳነ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ መሳፍንት 3