ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34
  35. 35
  36. 36
  37. 37
  38. 38
  39. 39
  40. 40
  41. 41
  42. 42
  43. 43
  44. 44
  45. 45
  46. 46
  47. 47
  48. 48

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሕዝቅኤል 45 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

የምድሪቱ አከፋፈል

1. ‘ “ምድሪቱን ርስት አድርጋችሁ በዕጣ በምትከፋፈሉበት ጊዜ፣ ርዝመቱ ሃያ አምስት ሺህ ክንድ፣ ወርዱ ሃያ ሺህ ክንድ የሆነውን አንዱን ክፍል፣ ለእግዚአብሔር የተቀደሰ ስፍራ አድርጋችሁ ስጡ፤ ስፍራውም በሙሉ ቅዱስ ይሆናል፤

2. ከዚሁም አምስት መቶ ክንድ በአምስት መቶ ክንድ፣ ዙሪያው አምሳ ክንድ ባዶ ቦታ ቀርቶ፣ ለመቅደሱ ይሁን።

3. ከተቀደሰውም ስፍራ ላይ ርዝመቱ ሃያ አምስት ሺህ ክንድ፣ ወርዱም ዐሥር ሺህ ክንድ ለካ፤ በዚህም ውስጥ መቅደሱ፣ ይኸውም ቅድስተ ቅዱሳኑ ይሆናል።

4. ይህም በቤተ መቅደሱ ውስጥ ለሚያገለግሉና፣ በእግዚአብሔር ፊት ለአገልግሎት ለሚቀርቡ ካህናት፣ ቅዱስ የሆነ የምድሪቱ ክፍል ይሆናል።

5. ርዝመቱ ሃያ አምስት ሺህ ክንድ፣ ወርዱ ዐሥር ሺህ ክንድ ስፋት ያለው ስፍራ መኖሪያ ከተሞቻቸውን እንዲከትሙ በቤተ መቅደስ ለሚያገለግሉ ሌዋውያን ርስት ይሆናል።

6. ‘ “ከተቀደሰው ስፍራ ጋር የተያያዘ ወርዱ አምስት ሺህ ክንድ፣ ርዝመቱ ሃያ አምስት ሺህ ክንድ የሆነ ቦታ ለከተማዪቱ ርስት አድርገህ ስጥ፤ ይህም ለመላው የእስራኤል ቤት ይሆናል።

7. ‘ “ገዡ ከቅዱሱ ስፍራና ከከተማው ወሰን ግራና ቀኝ ርስት ይኖረዋል፤ ይህም ከምዕራብ በኩል ወደ ምዕራብ አቅጣጫ ምሥራቅ በመዝለቅ፣ ከምዕራብ እስከ ምሥራቅ ያለውን ወሰን ርዝመት ተከትሎ ለአንዱ ነገድ ከተሰጠው ርስት ጋር ጐን ለጐን ይሄዳል።

8. ይህም መሬት በእስራኤል ምድር የገዡ ርስት ይሆናል። ከእንግዲህ ገዦቼ ሕዝቤን አይጨቍኑም፤ ነገር ግን የእስራኤል ቤት በየነገዳቸው ርስት እንዲይዙ ይፈቅዱላቸዋል።

9. ‘ “ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘የእስራኤል ገዦች ሆይ! ከልክ ዐልፋችኋል፤ ይብቃችሁ፤ ዐመፅንና ጭቈናን ተዉ፤ ቀናና ትክክል የሆነውን ነገር አድርጉ። የሕዝቤን ርስት መቀማት ይቅርባችሁ፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።

10. ትክክለኛ ሚዛን ትክክለኛ ኢፍና ትክክለኛ ባዶስ ይኑራችሁ።

11. የኢፍና የባዶሱ መመዘኛ ተመሳሳይ ይሁን፤ አንድ ባዶስ የሆመር አንድ ዐሥረኛ እንዲሁም አንድ ኢፍ የሆመር አንድ ዐሥረኛ ይሆናል፤ ሆመር ለሁለቱም ሚዛኖች መደበኛ መለኪያ ነው።

12. አንድ ሰቅል ሃያ ጌራህ የሚይዝ ይሆናል፤ በሃያ ሰቅል ላይ ሃያ አምስት ሰቅልና ዐሥራ አምስት ሰቅል ሲጨመር አንድ ምናን ይሆናል።’

ልዩ ልዩ መሥዋዕትና በዓላት

13. ‘ “የምታቀርቡት ልዩ መባ ይህ ነው፤ ከአንድ ሆመር መስፈሪያ ስንዴ አንድ ስድስተኛ ኢፍ እንዲሁም ከእያንዳንዱ ሆመር ገብስ አንድ ስድስተኛ ኢፍ ነው።

14. ዘይቱ በባዶስ ሲለካ የተወሰነው መስፈሪያ ከእያንዳንዱ ሆመር አንድ ዐሥረኛ ባዶስ ይሆናል፤ ይኸውም ዐሥር ባዶስ ወይም አንድ ሆመር ነው፤ ዐሥር ባዶስ ከአንድ ሆመር ጋር እኩል ነውና።

15. እንዲሁም ውሃ ከጠገበው ከእስራኤል መሰማሪያ፣ ሁለት መቶ በግ ካለው ከእያንዳንዱ መንጋ አንድ በግ ይውሰድ። ይህ ሁሉ ለሕዝቡ ማስተስረያ ለሚሆነው ለእህል ቍርባን፣ ለሚቃጠል መሥዋዕትና ለኅብረት መሥዋዕት ይውላል፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።

16. የምድሪቱ ሕዝብ ሁሉ ይህን ልዩ መባ ለእስራኤል ገዥ ይሰጣሉ።

17. በበዓላት፣ በወር መባቻና በሰንበታት፣ ለእስራኤል ቤት በተወሰኑት በዓላት ሁሉ የሚቃጠል መሥዋዕት፣ የእህል ቍርባንና የመጠጥ ቍርባን ማቅረብ የገዡ ኀላፊነት ነው፤ ለእስራኤል ቤት ማስተስረያ እንዲሆንም የኀጢአት መሥዋዕት፣ የእህል ቍርባን፣ የሚቃጠል መሥዋዕትና የኅብረት መሥዋዕት ያቀርባል።’

18. “ ‘ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘በመጀመሪያው ወር፣ በመጀመሪያው ቀን ነውር የሌለበትን ወይፈን ውሰድ፤ መቅደሱንም አንጻው።

19. ካህኑም ከኀጢአቱ መሥዋዕት ደም በመውሰድ በቤተ መቅደሱ በር መቃኖች፣ በመሠዊያው ላይኛ ዕርከን አራት ማእዘንና በውስጠኛው አደባባይ በር መቃኖች ላይ ይርጨው።

20. አንድ ሰው ሳያስብ ወይም ባለማወቅ ኀጢአት ቢሠራ፤ ወር በገባ በሰባተኛው ቀን ይህን ታደርጋለህ፤ በዚህ ዐይነት ለቤተ መቅደሱ ታስተሰርያላችሁ።’

21. “ ‘በመጀመሪያው ወር በዐሥራ አራተኛው ቀን የፋሲካን በዓል ታከብራላችሁ፤ ይህም እርሾ የሌለበትን እንጀራ የምትበሉበት ሰባት ቀን የሚከበር በዓል ነው።

22. በዚያም ቀን ገዢው ስለ ራሱና ስለ ምድሪቱ ሕዝብ ሁሉ አንድ ወይፈን የኀጢአት መሥዋዕት አድርጎ ያቀርባል።

23. በዓሉ በሚከበርበት በሰባቱ ቀን ገዡ በየዕለቱ እንከን የሌለባቸውን ሰባት ወይፈኖችና ሰባት አውራ በጎች የሚቃጠል መሥዋዕት አድርጎ ለእግዚአብሔር ያቅርብ፤ በየዕለቱም ለኀጢአት መሥዋዕት አውራ ፍየል ያቅርብ።

24. ለአንዱ ወይፈን አንድ የኢፍ መስፈሪያ፣ ለአንድ አውራ በግ አንድ የኢፍ መስፈሪያ የእህል ቍርባን አድርጎ፣ ለእያንዳንዱም ኢፍ አንድ የኢን መስፈሪያ ዘይት አብሮ ያቅርብ።