ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሕዝቅኤል 40:20-27 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

20. ከዚያም በሰሜን ትይዩ ያለውን፣ ወደ ውጩ አደባባይ የሚያመራውን በር ርዝመትና ወርድ ለካ።

21. እንደ መጀመሪያው በር ሁሉ ይኸኛውም በየጐኑ ያሉት ሦስት ሦስት የዘብ ቤቶች፣ በየመካከሉ ወጣ ወጣ ያሉ ግንቦችና መተላለፊያ በረንዳዎቹ መጠናቸው እኩል ነበር። ርዝመቱ አምሳ ክንድ፣ ወርዱም ሃያ አምስት ክንድ ነበር።

22. መስኮቶቹ፣ መተላለፊያ በረንዳዎቹና የዘንባባ ዛፍ ቅርጾቹ ልካቸው በምሥራቁ በር ካሉት ጋር ተመሳሳይ ነበር። ወደዚያ የሚያመሩ ሰባት ደረጃዎች አሉ፤ መተላለፊያ በረንዳዎቹም ከእነርሱ ጋር ትይዩ ነበር።

23. ልክ በምሥራቅ በኩል እንዳለው ሁሉ፣ ከሰሜኑ በር ጋር ትይዩ የሆነ ወደ ውስጠኛው አደባባይ የሚያመራ በር አለ። ከአንዱ በር እስከ ሌላኛው በር ያለውን ለካው፤ ይህም አንድ መቶ ክንድ ነበር።

24. ከዚያም ወደ ደቡብ አቅጣጫ መራኝ፤ እዚያም ፊቱን ወደ ደቡብ ያደረገ በር አየሁ፤ እርሱም የውስጠኛውን ግድግዳና መተላለፊያ በረንዳውን ለካ፤ የእነዚህም መጠን እንደ ሌሎቹ በሮች ነበር።

25. የመግቢያው በርና መተላለፊያ በረንዳው እንደ ሌሎቹ ሁሉ በዙሪያው ጠባብ መስኮቶች ነበሩት፤ ርዝመቱ አምሳ ክንድ፤ ወርዱም ሃያ አምስት ክንድ ነበር።

26. ከመተላለፊያ በረንዳው ትይዩ የሆኑ ሰባት ደረጃዎች ወደ መግቢያው በር ያመራሉ፤ ወጣ ወጣ ብለው በሚታዩ ግድግዳዎችም ላይ የዘንባባ ቅርጽ አለ።

27. ውስጠኛው አደባባይ ደግሞ ከደቡብ ጋር ትይዩ የሆነ በር አለው፤ እርሱም ከዚህ በር አንሥቶ በደቡብ አቅጣጫ እስካለው እስከ ውጭው በር ድረስ ለካው፤ ይህም አንድ መቶ ክንድ ሆነ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሕዝቅኤል 40