ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሕዝቅኤል 32:8-20 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

8. በሰማይ የሚያበሩትን ብርሃናት ሁሉ፣በአንተ ላይ አጨልማለሁ፤በምድርህ ላይ ጨለማን አመጣለሁ፤ይላል ጌታ እግዚአብሔር።

9. በማታውቀው ምድር፣በሕዝቦች መካከል ያንተን ጥፋት ሳመጣ፣የብዙ ሕዝብን ልብ አስጨንቃለሁ።

10. ሕዝቦች በአንተ ላይ ከደረሰው የተነሣ እንዲደነግጡ አደርጋለሁ፤ሰይፌን በፊታቸው ስነቀንቅ፣በአንተ ላይ ከደረሰው ሁኔታ የተነሣ ንጉሦቻቸው ይንቀጠቀጣሉ።አንተ በምትወድቅበት ቀን፣እያንዳንዳቸው ስለ ራሳቸው ሕይወት በመፍራት፣በየቅጽበቱ ይርበደበዳሉ።

11. “ ‘ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና፤“ ‘የባቢሎን ንጉሥ ሰይፍ፣በአንተ ላይ ይመጣል።

12. ከሕዝቦች ሁሉ እጅግ ጨካኝ በሆኑት፣በኀያላን ሰዎች ሰይፍ፣ያከማቸኸው ሰራዊት እንዲወድቅ አደርጋለሁ፤የግብፅን ኵራት ያንኰታኵታሉ፤የሰራዊቷም ብዛት ይጠፋል፤

13. ብዙ ውሃ ባለበት አጠገብ ያለውን፣የከብት መንጋዋን አጠፋለሁ፤ከእንግዲህ የሰው እግር አይረጋግጠውም፤የከብትም ኮቴ አያደፈርሰውም።

14. ከዚያም ውሆቿን አጠራለሁ፤ወንዞቿም እንደ ዘይት እንዲፈሱ አደርጋለሁ፤ይላል ጌታ እግዚአብሔር።

15. ግብፅን ባድማ ሳደርጋት፣ምድሪቱም ያላትን ሁሉ ያጣች ስትሆን፣በዚያም የሚኖሩትን ሁሉ ስመታ፣ያን ጊዜ እኔ እግዚአብሔር እንደሆንሁ ያውቃሉ።”

16. “ስለ እርሷ የሚያወርዱት ሙሾ ይህ ነው፤ የሕዝቦች ሴት ልጆች ያዜሙታል፤ ስለ ግብፅና ስለ ብዙ ሰራዊቷ ሁሉ ሙሾ ያወርዳሉ፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።”

17. በዐሥራ ሁለተኛው ዓመት፣ ከወሩም በዐሥራ አምስተኛው ቀን የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣ፤

18. “የሰው ልጅ ሆይ፤ ስለ ብዙው የግብፅ ሰራዊት አልቅስ፤ እርሷንና የኀያላንን ሕዝቦች ሴት ልጆች ወደ ጒድጓድ ከሚወርዱት ጋር ከምድር በታች አውርዳቸው።

19. እንዲህም በላቸው፤ ‘እናንተ ከሌሎች የተለያችሁ ናችሁን? ውረዱ፤ ባልተገረዙትም መካከል ተጋደሙ።’

20. እነርሱም በሰይፍ በተገደሉት መካከል ይወድቃሉ፤ ሰይፉ ተመዟል፤ ከብዙ ሰራዊቷ ሁሉ ጋር ትጐተት።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሕዝቅኤል 32