ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14
  15. 15
  16. 16
  17. 17
  18. 18
  19. 19
  20. 20
  21. 21
  22. 22
  23. 23
  24. 24
  25. 25
  26. 26
  27. 27
  28. 28
  29. 29
  30. 30
  31. 31
  32. 32
  33. 33
  34. 34
  35. 35
  36. 36
  37. 37
  38. 38
  39. 39
  40. 40
  41. 41
  42. 42
  43. 43
  44. 44
  45. 45
  46. 46
  47. 47
  48. 48

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሕዝቅኤል 23 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

ሁለቱ ዘማውያት እኅትማማቾች

1. የእግዚአብሔር ቃል እንዲህ ሲል ወደ እኔ መጣ፤

2. “የሰው ልጅ ሆይ፤ ከአንድ እናት የተወለዱ ሁለት ሴቶች ልጆች ነበሩ፤

3. ገና በወጣትነታቸው ዘማውያት በመሆን በግብፅ ሳሉ አመነዘሩ፤ በዚያችም ምድር አጐጠጐጤአቸው ተዳበሰ፤ የድንግልናቸውም ጒያ በእጅ ተሻሸ።

4. የታላቂቱ ስም ኦሖላ፣ የእኅቷም ኦሖሊባ ነበር፤ ሁለቱም የእኔ ሆኑ፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆችም ወለዱ። ስማቸውም፣ ኦሖላ ሰማርያ ናት፤ ኦሖሊባም ኢየሩሳሌም።

5. “ኦሖላ የእኔ ሆና ሳለ በእኔ ላይ አመነዘረች፤ ጦረኞች ከሆኑት ጎረቤቶቿ ከአሦራውያን ውሽሞቿ ጋር ሴሰነች፤

6. እነርሱም ሐምራዊ የለበሱ፣ ገዦችና አዛዦች፣ ሁሉም መልከ ቀና ጐበዛዝትና ፈጣን ፈረሰኞች ነበሩ።

7. እርሷ በዝሙት ራሷን ምርጥ ለሆኑት አሦራውያን ሁሉ አሳልፋ ሰጠች፤ አብረዋት ባመነዘሩት ሰዎች ጣዖት ሁሉ ረከሰች።

8. በግብፅ የጀመረችውን አመንዝራነቷን አልተወችም፤ በዚያ ወንዶች በወጣትነቷ ከእርሷ ጋር ተኙ፤ የድንግልናዋን ጡት አሻሹ፤ ፍትወታቸውን አፈሰሱባት።

9. “ስለዚህ አብራቸው ላመነዘረች ለአሦራውያን ውሽሞቿ አሳልፌ ሰጠኋት።

10. እነርሱም ዕርቃን አስቀሯት፤ ወንዶችና ሴቶች ልጆቿን ነጠቋት፤ እርሷንም በሰይፍ ገደሏት፤ በሴቶችም ዘንድ መተረቻ ሆና ቀረች፤ ፍርድም ተፈጸመባት።

11. “እኅቷ ኦሖሊባ ይህን አይታ ነበር፤ ሆኖም በፍትወቷና በዘማዊነቷ ከእኅቷ የባሰች ብልሹ ሆነች።

12. ደግሞም ገዦችና አዛዦች፣ ጌጠኛ ልብስ የለበሱ ጦረኞች፣ ፈጣን ፈረሰኞችና፣ ሁሉም መልከ ቀና ከሆኑት አሦራውያን ጐበዛዝት ጋር አመነዘረች።

13. ይህችም እንደ ረከሰች አየሁ፤ ሁለቱም በአንድ መንገድ ሄዱ።

14. “በአመንዝራነቷ እየባሰች ሄደች፤ በደማቅ ቀይ ቀለም በግድግዳ ላይ የተቀረጹ የከለዳውያንን ወንዶች ምስል አየች፤

15. እነርሱም ወገባቸውን በቀበቶ የታጠቁና በራሳቸው ላይ ተንጠልጣይ ያለው ጥምጥም የጠመጠሙ ነበሩ፤ ሁሉም የከለዳውያን ተወላጆችና የባቢሎን ሠረገላ አዛዦች ይመስሉ ነበር።

16. ባየቻቸውም ጊዜ በፍትወት ተቃጠለች፤ ወደ ከላውዴዎን መልእክተኞች ላከችባቸው።

17. ባቢሎናውያንም መጥተው ወደ ፍቅር መኝታዋ ገቡ፤ በፍትወታቸውም አረከሷት፤ እርሷም በእነርሱ ከረከሰች በኋላ ጠልታቸው ከእነርሱ ዘወር አለች።

18. ግልሙትናዋን በአደባባይ በፈጸመችና ዕርቃን በገለጠች ጊዜ ከእኅቷ ዘወር እንዳልሁ፣ ጠልቼአት ከእርሷም ዘወር አልሁ።

19. እርሷ ግን በግብፅ ያመነዘረችበት የወጣትነት ዘመኗ ትዝ እያላት የባሰ ዘማዊት ሆነች።

20. በዚያም አባለዘራቸው እንደ አህያ፣ የዘር ፍሰታቸውም እንደ ድንጒላ ፈረስ ዘር ፍሰት ከሆነ ውሽሞቿ ጋር አመነዘረች፤

21. በግብፅ ምድር ጒያሽን የታሸሽበትንና የወጣትነት ጡቶችሽን የተዳበስሽበትን የኰረዳነትሽን ብልግና ተመኘሽ።

22. “ስለዚህ፣ ኦሖሊባ ሆይ፤ ጌታእግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘ጠልተሻቸው ከእነርሱ ዘወር ያልሽውን ውሽሞችሽን በአንቺ ላይ አስነሣለሁ፤ እነርሱንም ከየአቅጣጫው አመጣብሻለሁ፤

23. እነርሱም ባቢሎናውያንና ከለዳውያን ሁሉ፣ የፋቁድ፣ የሱሔና የቆዓ ሰዎች፣ ከእነርሱም ጋር አሦራውያን ሁሉ ናቸው። እነዚህም መልከ ቀና ጐበዛዝት ሲሆኑ፣ ሁላቸውም በፈረስ ላይ የተቀመጡ ገዦችና አዛዦች፣ የሠረገላ አዛዦችና ከፍተኛ ባለ ሥልጣኖች ነበሩ።

24. እነርሱም የጦር መሣሪያ፣ ሠረገላና ጋሪ በመያዝ ብዙ ሕዝብ ሆነው ይመጡብሻል፤ ትላልቅና መለስተኛ ጋሻ በማንገብና የራስ ቍር በመድፋት በየአቅጣጫው ይሰለፉብሻል፤ እኔም ለፍርድ በእጃቸው አሳልፌ እሰጥሻለሁ፤ በሕጋቸውም መሠረት ይቀጡሻል።

25. የቅናት ቍጣዬን በአንቺ ላይ አመጣለሁ፤ እነርሱም በአንቺ ላይ በቍጣ ይወጣሉ፤ አፍንጫሽንና ጆሮሽን ይቈርጣሉ፤ ከአንቺ ወገን የተረፉትም በሰይፍ ይወድቃሉ። ወንዶችና ሴቶች ልጆችሽን ይወስዱብሻል፤ የተረፉትንም እሳት ይበላቸዋል።

26. ልብስሽን ይገፉሻል፤ ምርጥ ጌጣጌጥሽንም ይወስዱብሻል።

27. በግብፅ የጀመርሽውን ብልግናና ሴሰኝነት ከአንቺ አስወግዳለሁ፤ አንቺም ዐይንሽን ወደ እነዚህ አታነሺም፤ ከእንግዲህ ግብፅን አታስቢም።

28. “ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላልና፤ ‘እነሆ ተጸይፈሻቸው ከእነርሱ ዘወር ላልሽው ለጠላሻቸው አሳልፌ እሰጥሻለሁ።

29. እነርሱም በጥላቻ ይቀርቡሻል፤ የለፋሽበትንም ሁሉ ይቀሙሻል፤ ከማሕፀን እንደ ወጣሽ ዕርቃንሽን ያስቀሩሻል፤ የሴሰኝነትሽ ኀፍረት ይገለጣል። ብልግናሽና ገደብ የለሽ ርኵሰትሽ፣

30. ይህን አምጥተውብሻል፤ ከአሕዛብ ጋር በማመንዘር በጣዖቶቻቸው ረክሰሻልና።

31. በእኅትሽ መንገድ ስለ ሄድሽ የእርሷን ጽዋ በእጅሽ አስጨብጥሻለሁ።’

32. “ጌታእግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤“ሰፊና ጥልቅ የሆነውን ጽዋ፣የእኅትሽን ጽዋ ትጠጪአለሽ፤ብዙም ስለሚይዝ ስድብና ነቀፌታትጠግቢአለሽ።

33. በእኅትሽ በሰማርያ ጽዋ፣በመፍረስና በጥፋት ጽዋ፣በስካርና በሐዘን ትሞዪአለሽ።

34. ትጠጪዋለሽ፤ ትጨልጪዋለሽም፤ከዚያም ጽዋውን ትሰባብሪዋለሽ፤ጡትሽንም ትቈራርጪአለሽ፤እኔ ተናግሬአለሁ፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።

35. “ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘ረስተሽኛል፤ ወደ ኋላም ገሸሽ አድርገሽኛልና የብልግናሽንና የሴሰኝነትሽን ውጤት ትሸከሚአለሽ።’

36. እግዚአብሔር እንዲህ አለኝ፤ “የሰው ልጅ ሆይ፤ በኦሖላና በኦሖሊባ ትፈርዳለህን? እንግዲያውስ ጸያፍ ተግባራቸውን ንገራቸው።

37. አመንዝረዋል እጃቸውም በደም ተበክሎአልና። ከጣዖቶቻቸው ጋር አመነዘሩ፤ የወለዱልኝን ልጆቻቸውን እንኳ ለእነርሱ መብል ይሆኑ ዘንድ በእሳት ሠውተውላቸዋል።

38. ደግሞም ይህን አደረጉብኝ፤ በዚያኑ ቀን ቤተ መቅደሴን አረከሱ፤ ሰንበታቴንም አቃለሉ።

39. ልጆቻቸውን ለጣዖቶቻቸው በሠዉባት ዕለት ወደ መቅደሴ ገብተው አረከሷት፤ እንግዲህ በቤቴ ውስጥ ያደረጉት እንዲህ ያለውን ነው።

40. “ከዚህም በላይ ወንዶች ከሩቅ እንዲመጡላቸው መልእክተኛ ላኩ፤ እነርሱም መጡ። አንቺም ገላሽን ታጥበሽ፣ ዐይንሽን ተኵለሽና በጌጣጌጥ ተውበሽ ጠበቅሻቸው።

41. በተዋበ ዐልጋ ላይ ተቀመጥሽ፤ ዕጣኔንና ዘይቴን ያኖርሽበትንም ጠረጴዛ ከዐልጋው ፊት ለፊት አደረግሽ።

42. “የሚፈነጥዙ ሰዎች ድምፅ በዙሪያዋ ነበር፤ ከሚያውኩ ሰዎች ጋር ከበረሓ የመጡ ሰካራሞች ነበሩ፤ በሴትየዋና በእኅትዋም ላይ አንባር፣ በራሳቸውም ላይ የተዋበ አክሊል አደረጉላቸው።

43. እኔም በአመንዝራነት ሰውነቷ ስላለቀው፣ ‘እርሷ ሕይወቷ ይኸው ስለ ሆነ እንደ ዝሙት ዐዳሪ ይጠቀሙባት’ አልሁ።

44. እነርሱም ከእርሷ ጋር ተኙ፤ ሰው ከአመንዝራ ሴት ጋር እንደሚተኛ ከእነዚያ ባለጌ ሴቶች፣ ከኦሖላና ከኦሖሊባ ጋር ተኙ።

45. ጻድቃን ግን ለአመንዝራና ለነፍሰ ገዳይ ሴቶች የሚገባቸውን ፍርድ ይፈርዱባቸዋል። አመንዝሮች ናቸውና፤ እጃቸውም በደም ተበክሎአል።

46. “ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘ሕዝብን ቀስቅሰህ አምጣባቸው፤ ለሽብርና ለዝርፊያም አሳልፈህ ስጣቸው።

47. ሕዝቡ በድንጋይ ይወግራቸዋል፤ በገዛ ሰይፋቸው ይቈራ ርጣቸዋል፤ ወንድና ሴት ልጆቻቸውን ይገድላል፤ ቤቶቻቸውንም ያቃጥላል።

48. “ ‘ስለዚህ ሴቶች ሁሉ እንዲጠነቀቁና መጥፎ ፈለጋችሁን እንዳይከተሉ፣ ሴሰኝነትን ከምድሪቱ አጠፋለሁ።

49. የሴሰኝነታችሁን ዋጋ ታገኛላችሁ፤ ጣዖት በማምለክ ለፈጸማችሁት ኀጢአት ቅጣት ትሸከማላችሁ፤ በዚያን ጊዜ እኔ ጌታ እግዚአብሔር እንደሆንሁ ታውቃላችሁ።’ ”