ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሕዝቅኤል 11:1-12 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. መንፈስም ወደ ላይ አነሣኝ፤ ከዚያም በምሥራቅ በኩል ወዳለው ወደ እግዚአብሔር ቤት በር አመጣኝ። በበሩም መግቢያ ላይ ሃያ አምስት ሰዎች ነበሩ፤ በእነርሱም መካከል የሕዝቡን መሪዎች የዓዙርን ልጅ ያእዛንያንና የበናያስን ልጅ ፈላጥያንን አየሁ።

2. እግዚአብሔርም እንዲህ አለኝ፤ “የሰው ልጅ ሆይ፤ እነዚህ ሰዎች ክፋትን የሚያቅዱና በዚህችም ከተማ ላይ ተንኰልን የሚመክሩ ናቸው።

3. እነርሱም፣ “ቤቶች የሚሠሩበት ጊዜ ቅርብ አይደለምን? ይህች ከተማ ድስት ናት፤ እኛም ሥጋ ነን’ ብለዋል።

4. ስለዚህ ትንቢት ተናገርባቸው፤ የሰው ልጅ ሆይ፤ ትንቢት ተናገር።”

5. የእግዚአብሔርም መንፈስ በላዬ ወረደ እንዲህም አለኝ፤ “እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘የእስራኤል ቤት ሆይ፤ እናንተ እንዲህ ብላችኋል፤ እኔ ግን የልባችሁን ሐሳብ ዐውቃለሁ።

6. በዚህች ከተማ ብዙ ሰው ገድላችኋል፤ መንገዶቿንም ሬሳ በሬሳ አድርጋችኋል።’

7. “ስለዚህ ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘በዚያ የጣላችኋቸው ሬሳዎች እነርሱ ሥጋ ናቸው፤ ይህችም ከተማ ድስት ናት፤ እናንተን ግን ከውስጧ አወጣችኋለሁ።

8. ሰይፍን ፈርታችኋል፤ እኔም ሰይፍ እልክባችኋለሁ፤ ይላል ጌታ እግዚአብሔር።

9. ከከተማዪቱ አውጥቼ ለባዕዳን አሳልፌ እሰጣችኋለሁ፤ ፍርድንም አመጣባችኋለሁ።

10. በሰይፍ ትወድቃላችሁ፤ በእስራኤል ድንበር ላይ እፈርድባችኋለሁ፤ በዚያ ጊዜም እኔ እግዚአብሔር እንደሆንሁ ታውቃላችሁ።

11. ይህች ከተማ ድስት አትሆንላችሁም፤ እናንተም በውስጧ ሥጋ አትሆኑም፤ በእስራኤልም ድንበር ላይ እፈርድባችኋለሁ፤

12. በዚያ ጊዜ እኔ እግዚአብሔር እንደሆንሁ ታውቃላችሁ፤ እናንተ በዙሪያችሁ ያሉትን አሕዛብ ሥርዐት ተከተላችሁ እንጂ ትእዛዜን አልፈጸማችሁም ሕጌንም አልጠበቃችሁምና።”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ ሕዝቅኤል 11