ምዕራፎች

  1. 1
  2. 2
  3. 3
  4. 4
  5. 5
  6. 6
  7. 7
  8. 8
  9. 9
  10. 10
  11. 11
  12. 12
  13. 13
  14. 14

ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

ሆሴዕ 1 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. በይሁዳ ነገሥታት በዖዝያን፣ በኢዮአታም፣ በአካዝና በሕዝቅያስ ዘመን እንዲሁም በእስራኤል ንጉሥ በዮአስ ልጅ በኢዮርብዓም ዘመን ወደ ብኤሪ ልጅ ወደ ሆሴዕ የመጣው የእግዚአብሔር ቃል ይህ ነው፤

የሆሴዕ ሚስትና ልጆቹ

2. እግዚአብሔር በሆሴዕ መናገር በጀመረ ጊዜ፣ እግዚአብሔር “ምድሪቱ ከእግዚአብሔር ተለይታ ታላቅ ምንዝርና እያደረገች ስለ ሆነ፣ ሄደህ አመንዝራ ሴት አግባ፤ የምንዝርና ልጆችንም ለራስህ ውሰድ” አለው።

3. ስለዚህ እርሱ የዴቤላይምን ሴት ልጅ ጎሜርን አገባ፤ እርሷም ፀነሰች፤ ወንድ ልጅም ወለደችለት።

4. እግዚአብሔርም ሆሴዕን እንዲህ አለው፤ “በኢይዝራኤል ስለ ተፈጸመው ግድያ የኢዩን ቤት በቅርቡ ስለምቀጣና የእስራኤልንም መንግሥት እንዲያከትም ስለማደርግ፣ ስሙን ኢይዝራኤል ብለህ ጥራው።

5. በዚያም ቀን በኢይዝራኤል ሸለቆ፣ የእስራኤልን ቀስት እሰብራለሁ።”

6. ጎሜር እንደ ገና ፀነሰች፤ ሴት ልጅም ወለደች፤ እግዚአብሔርም ሆሴዕን እንዲህ አለው፤ “ይቅር እላቸው ዘንድ ለእስራኤል ቤት ከእንግዲህ ስለማልራራላቸው፣ ስሟን ሎሩሃማ ብለህ ጥራት።

7. ነገር ግን ለይሁዳ ቤት እራራለሁ፤ በቀስት ወይም በሰይፍ ወይም በጦርነት ወይም በፈረሶችና በፈረሰኞች ሳይሆን በአምላካቸው በእግዚአብሔር አድናቸዋለሁ።”

8. ጎሜር፣ ሎሩሃማን ጡት ካስጣለች በኋላ ሌላ ወንድ ልጅ ወለደች።

9. እግዚአብሔርም እንዲህ አለው፤ “ሎዓሚ ብለህ ጥራው፤ ምክንያቱም እናንተ ሕዝቤ አይደላችሁም፤ እኔም አምላካችሁ አይደለሁምና።

10. “ይሁን እንጂ እስራኤላውያን ሊሰፈርና ሊቈጠር እንደማይችል እንደ ባሕር አሸዋ ይሆናሉ፤ ‘ሕዝቤ አይደላችሁም’ በተባሉበት ቦታ፣ ‘የሕያው አምላክ ልጆች’ ተብለው ይጠራሉ።

11. የይሁዳ ሕዝብና የእስራኤል ሕዝብ እንደ ገና አንድ ይሆናሉ አንድ መሪም ይሾማሉ፤ አንድ ሆነውም በምድሪቱ ይገናሉ፤ የኢይዝራኤል ቀን ታላቅ ይሆናልና።