ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ዜና መዋዕል 6:20-32 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

20. ስምህ እንደሚጠራበት ወደ ተናገርኸው ወደዚህ ቤተ መቅደስ ዓይኖችህ በቀንም በሌሊትም የተገለጡ ይሁኑ፤ ባሪያህ ወደዚህ ስፍራ የሚጸልየውንም ጸሎት ስማ።

21. ባሪያህና ሕዝብህ እስራኤል ወደዚህ ስፍራ በሚጸል ዩበትም ጊዜ ልመናቸውን ስማ፤ ከማደሪያህ ከሰማይ ስማ፤ ሰምተህም ይቅር በል።

22. አንድ ሰው ባልንጀራውን ቢበድልና እንዲምል ቢጠየቅ፣ እርሱም መጥቶ በቤተ መቅደሱ በመሠዊያህ ፊት ቢምል፣

23. ከሰማይ ሆነህ ስማ፤ አድርግም። በደለኛውን፣ በደሉን በራሱ ላይ አድርገህ እንደ ሥራው በመክፈል በባሪያዎችህ መካከል ፍረድ። ንጹሑም በደለኛ አለመሆኑን አስታውቅ፤ እንደ ንጽሕናውም ክፈለው።

24. “ሕዝብህ እስራኤል አንተን ከመበደላቸው የተነሣ በጠላቶቻቸው ፊት ድል ቢሆኑ፣ ወደ አንተ ተመልሰውም በዚህ ቤተ መቅደስ ውስጥ በፊትህ በመጸለይና ልመናቸውን በማቅረብ ስምህን ቢጠሩ፣

25. በሰማይ ሆነህ ስማ፤ የሕዝብህን የእስራኤልን ኀጢአት ይቅር በል፤ ለእነርሱና ለአባቶቻቸው ወደ ሰጠሃቸውም ምድር መልሳቸው።

26. “ሕዝብህ አንተን ከመበደላቸው የተነሣ፣ ሰማያት ተዘግተው ዝናብ ባይዘንብ፣ አንተ ስለአስጨነቅሃቸው ወደዚህ ስፍራ ቢጸልዩ፣ ስምህን ቢጠሩና ከኀጢአታቸው ቢመለሱ፣

27. በሰማይ ሆነህ ስማ፤ የባሪያዎችህን የሕዝብህን የእስራኤልን ኀጢአት ይቅር በል፤ የሚኖሩበትን ቀናውን መንገድ አስተምራቸው፤ ለሕዝብህ ርስት አድርገህ በሰጠኸውም ምድር ላይ ዝናብን ላክ።

28. “በምድሪቱ ላይ ራብ ወይም ቸነፈር ወይም ዋግ ወይም አረማሞ ወይም አንበጣ ወይም ኩብኩባ በሚወርድባት ጊዜ፣ ወይም ደግሞ በየትኛውም ከተማቸው ሳሉ ጠላት በሚከባቸው ጊዜ፣ ወይም ማናቸውም አደጋ ወይም ደዌ በሚደርስባቸው ጊዜ፣

29. ከሕዝብህ ከእስራኤል ማንም ሰው ጭንቀቱና ሕመሙ ተሰምቶት፣ እጁን ወደዚህ ቤተ መቅደስ በመዘርጋት ጸሎትና ልመና ቢያቀርብ፣

30. በሰማይ በማደሪያህ ሆነህ ስማ፤ ይቅርም በል፤ የሰውን ልብ የምታውቅ አንተ ብቻ ስለ ሆንህ ለእያንዳንዱ እንደ ሥራው መጠን ክፈለው፤

31. ይህም ለአባቶቻችን በሰጠሃቸው ምድር በሚኖሩበት ጊዜ ሁሉ አንተን እንዲፈሩህና በመንገዶችህ እንዲሄዱ ነው።

32. “ከሕዝብህ ከእስራኤል ወገን ያልሆነ ባዕድ ሰው ስለ ታላቁ ስምህ፣ ስለ ኀያሉ እጅህና ስለ ተዘረጋው ክንድህ ሰምቶ ከሩቅ አገር በመምጣት ወደዚህ ቤተ መቅደስ በሚጸልይበት ጊዜ፣

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ዜና መዋዕል 6