ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ዜና መዋዕል 15:8-18 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

8. አሳ ይህን ቃልና የነቢዩን የዖዴድን ልጅ የዓዛርያስን ትንቢት በሰማ ጊዜ በረታ። ከመላው ይሁዳና ከብንያም ምድር፣ በኤፍሬምም ኰረብታዎች ላይ ከያዛቸው ከተሞች አስጸያፊዎቹን ጣዖታት አስወገደ። ከእግዚአብሔር መቅደስ ሰበሰብ ፊት ለፊት የነበረውንም የእግዚአብሔር መሠዊያ አደሰ።

9. አምላኩ እግዚአብሔር ከእርሱ ጋር መሆኑን ባዩ ጊዜ፣ ከእስራኤል ብዙ ሰዎች እርሱን ተጠግተው ነበር፤ እርሱም ይሁዳንና ብንያምን እንዲሁም ከኤፍሬም፣ ከምናሴና ከስምዖን መጥተው ከእነርሱ ጋር የተቀመጡትን ሰበሰበ።

10. እነርሱም በአሳ ዘመነ መንግሥት በዐሥራ አምስተኛው ዓመት፣ በሦስተኛው ወር በኢየሩሳሌም ተሰበሰቡ።

11. በዚያን ጊዜ በምርኮ ካመጡት ውስጥ ሰባት መቶ በሬ፣ ሰባት ሺ በግና ፍየል ለእግዚአብሔር ሠዉ።

12. የአባቶቻቸውንም አምላክ እግዚአብሔርን በፍጹም ልባቸውና በፍጹም ነፍሳቸው ይሹ ዘንድ ቃል ኪዳን አደረጉ።

13. የእስራኤልን አምላክ እግዚአብሔርን የማይፈልግ ሁሉ ግን፣ ትንሽም ሆነ ትልቅ፣ ወንድም ሆነ ሴት እንዲገደል አደረጉ።

14. ይህንንም በታላቅ ድምፅ፣ በእልልታ፣ በእምቢልታና በመለከት ድምፅ ለእግዚአብሔር ማሉ።

15. በፍጹም ልባቸው ስለማሉም የይሁዳ ሕዝብ በመሐላው ደስ ተሰኙ። እግዚአብሔርን ከልብ ፈለጉት፤ እርሱም ተገኘላቸው፤ ስለዚህ እግዚአብሔር በሁሉም አቅጣጫ ዕረፍት ሰጣቸው።

16. እንዲሁም ንጉሥ አሳ አያቱን ማዓካን ለአስጸያፊዋ የአሼራ ጣዖት ዐምድ ስላቆመች ከእቴጌነት ክብሯ ሻራት። አሳም ዐምዱን ቈርጦ በመሰባበር በቄድሮን ሸለቆ አቃጠለው።

17. ምንም እንኳ ማምለኪያ ኰረብታዎችን ሙሉ በሙሉ ከእስራኤል ባያስወግድም፣ የአሳ ልብ በዘመኑ ሁሉ ፈጽሞ ለእግዚአብሔር የተገዛ ነበር።

18. እርሱና አባቱ የቀደሱትን ብሩን፣ ወርቁንና ልዩ ልዩ ዕቃ ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ አገባ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ዜና መዋዕል 15