ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ዜና መዋዕል 11:11-23 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

11. እነዚህንም ምሽጎቻቸውን አጠንክሮ፣ አዛዦችን ሾመባቸው፤ ምግብ፣ ዘይትና የወይን ጠጅ አከማቸባቸው።

12. በየከተሞቹም ሁሉ ጋሻና ጦር አከማችቶ ይበልጥ አጠና ከራቸው። በዚህ ዐይነት ይሁዳንና ቢንያምን የራሱ አደረገ።

13. በመላው እስራኤል ያሉት ካህናትና ሌዋውያን ከየክልላቸው ሁሉ ወደ እርሱ ተሰበሰቡ።

14. ኢዮርብዓምና ልጆቹ ሌዋውያኑን ከእግዚአብሔር የክህነት አገልግሎት ስላባረሯቸው ሌዋውያኑ ማሰማሪያ ቦታቸውንና ንብረታቸውን ሁሉ ትተው ወደ ይሁዳና ወደ ኢየሩሳሌም መጡ፤

15. እርሱም ለየኰረብታው መስገጃ እንዲሁም ለሠራቸው የፍየልና የጥጃ ምስሎች የራሱን ካህናት ሾመ።

16. ከእያንዳንዱም የእስራኤል ነገድ ከልባቸው የእስራኤልን አምላክ እግዚአብሔርን የሚፈልጉ ሁሉ፣ ለአባቶቻቸው አምላክ ለእግዚአብሔር መሥዋዕት ያቀርቡ ዘንድ፣ ሌዋውያኑን ተከትለው ወደ ኢየሩሳሌም ሄዱ።

17. በዚሁ ሁኔታ የዳዊትንና የሰሎሞንን መንገድ በመከተል፣ ለሦስት ዓመት የይሁዳን መንግሥት አበረቱ፤ የሰሎሞንን ልጅ ሮብዓምንም ረዱ።

18. ሮብዓም መሐላትን አገባ፤ አባቷ የዳዊት ልጅ ኢያሪሙት ሲሆን፣ እናቷም አቢካኢል የተባለች፣ የእሴይ የልጅ ልጅ የኤልያብ ልጅ ነበረች።

19. እርስዋም የዑስ፣ ሰማርያና ዛሃም የተባሉ ወንዶች ልጆች ወለደችለት።

20. ከዚያም የአቤሴሎምን ልጅ መዓካን አገባ፤ እርሷም አብያ፣ ዓታይ፣ ዚዛ፣ ሰሎሚት የተባሉትን ወለደችለት።

21. ሮብዓም መዓካን ከሌሎቹ ሚስቶቹና ቁባቶቹ ይልቅ አብልጦ ወደዳት። ባጠቃላይ ዐሥራ ስምንት ሚስትና ስልሣ ቁባት፣ ሃያ ስምንት ወንድና ሥልሳ ሴት ልጆች ነበሩት።

22. ሮብዓም የመዓካን ልጅ አባያን ሊያነግሠው ስለ ፈለገ ከልዑላን ወንድሞቹ አልቆ ዋና አደረገው።

23. ከወንዶች ልጆቹም ጥቂቱን በይሁዳና በብንያም አውራጃዎች እንዲሁም በተመሸጉት ከተሞች ስለ ሾማቸው፣ ዘዴኛነቱን አሳይቶአል። የሚያስፈልጋቸውን በብዛት ሰጣቸው፤ ብዙ ሚስቶችም አጋባቸው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ዜና መዋዕል 11