ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ነገሥት 16:12-20 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

12. ንጉሡ ከደማስቆ ተመልሶ በመጣ ጊዜ፣ መሠዊያውን አየ፤ ቀርቦም በመሠዊያው ላይ ወጣ፤

13. ከዚያም የሚቃጠል መሥዋዕቱንና የእህል ቊርባኑን በመሠዊያው ላይ አቀረበ፤ የመጠጥ ቊርባኑን አፈሰሰ፤ የኅብረት መሥዋዕቱንም ደም በመሠዊያው ላይ ረጨ።

14. በአዲሱ መሠዊያና በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ መካከል፣ በእግዚአብሔር ፊት ቆሞ የነበረውን የናስ መሠዊያ፣ ከቦታው አሥነስቶ ከአዲሱ መሠዊያ በስተ ሰሜን በኩል አኖረው።

15. ከዚያም ንጉሥ አካዝ፣ ካህኑን ኦርያን እንዲህ ሲል አዘዘው፤ “በዚህ በትልቁ አዲስ መሠዊያ ላይ የጧቱን የሚቃጠል መሥዋዕትና የማታውን የእህል ቊርባን፣ የንጉሡን የሚቃጠል መሥዋዕትና የእህሉን ቊርባን እንዲሁም የመላውን የአገሪቱን ሕዝብ የሚቃጠል መሥዋዕት፣ የእህልና የመጠጥ ቊርባናቸውን አቅርብ፤ የሚቃጠለውን መሥዋዕት ደምና የሌላውን መሥዋዕት ደም ሁሉ በመሠዊያው ላይ እርጨው፤ የናሱ መሠዊያ ግን እኔ መመሪያ ለመጠየቅ የምጠቀምበት ይሆናል።”

16. ካህኑ ኦርያም ንጉሡ አካዝ እንዳዘዘው ሁሉ እንዲሁ አደረገ።

17. ንጉሡ አካዝም የጐንና የጐን ሳንቃዎቹን ነቅሎ ወሰደ፤ በተንቀሳቃሹ መቆሚያ ላይ ያሉትን የመታጠቢያ ሳሕኖች አስወገደ። የውሃ ማጠራቀሚያውን ክብ ገንዳ ከታች ተሸክመው ከያዙት ከዐሥራ ሁለቱ የናስ ቅርጽ ኮርማዎች ላይ አውርዶ በጠፍጣፋ ድንጋይ ላይ አስቀመጠው።

18. የአሦርንም ንጉሥ ለማስደሰት ሲል፣ በዕለተ ሰንበት ንጉሣዊ ዙፋን እንዲዘረጋበት በቤተ መቅደሱ ውስጥ የተሠራውን ከፍ ያለ ስፍራና ነገሥታቱ ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ የሚገቡበትን በውጭ ያለውን መግቢያ አነሣ።

19. በአካዝ ዘመነ መንግሥት የተከናወነው ሌላው ሥራ፣ የፈጸመውም ሁሉ በይሁዳ ነገሥታት ታሪክ ተጽፎ የሚገኝ አይደለምን?

20. አካዝም ከአባቶቹ ጋር አንቀላፋ፤ ከእነርሱ ጋር በዳዊት ከተማ ተቀበረ። ልጁ ሕዝቅያስም በእግሩ ተተክቶ ነገሠ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ነገሥት 16