ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ሳሙኤል 24:5-15 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

5. ዮርዳኖስን ከተሻገሩ በኋላ፣ በሸለቆው ውስጥ ካለችው ከተማ በስተ ደቡብ በምትገኘው በአሮዔር አጠገብ ሰፈሩ፤ ከዚያም በጋድ በኩል አድርገው ወደ ኢያዜር ሄዱ፤

6. እንዲሁም ወደ ገለዓድና ወደተባሶን አዳሰይ፣ ቀጥሎም ወደ ዳንየዓን ከዚያም ዞረው ወደ ሲዶና ሄዱ።

7. ደግሞም ወደ ጢሮስ ምሽግ፣ ወደ ኤዊያውያንና ወደ ከነዓናውያን ከተሞች፣ በመጨረሻም በይሁዳ ደቡብ ወዳለችው ወደ ቤርሳቤህ ሄዱ።

8. ምድሪቱን ሁሉ ዞረው ከዘጠኝ ወር ከሃያ ቀን በኋላ ወደ ኢየሩሳሌም ተመለሱ።

9. ኢዮአብም የተዋጊዎቹን ጠቅላላ ቍጥር ለንጉሡ አሳወቀ፤ በእስራኤል ስምንት መቶ ሺህ፣ በይሁዳ አምስት መቶ ሺህ ሰይፍ መምዘዝ የሚችሉ ብቃት ያላቸው ሰዎች ተገኙ።

10. ዳዊት ተዋጊዎቹን ከቈጠረ በኋላ ኅሊናው ስለ ወቀሰው፣ “ባደረግሁት ነገር ታላቅ ኀጢአት ሠርቻለሁ፤ አሁንም እግዚአብሔር ሆይ፤ የአገልጋይህን በደል እንድታርቅ እለምንሃለሁ፤ የፈጸምሁት ታላቅ የስንፍና ሥራ ነውና” አለ።

11. በማግስቱ ጠዋት ዳዊት ከመነሣቱ በፊት የእግዚአብሔር ቃል የዳዊት ባለ ራእይ ወደ ሆነው ወደ ነቢዩ ወደ ጋድ መጣ፤

12. እንዲህም አለው፤ “ሂድና ዳዊትን፣ ‘እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ሦስት ነገሮችን ለምርጫ አቅርቤልሃለሁ፤ በአንተ ላይ አደርግብህ ዘንድ አንዱን ምረጥ’ በለው።”

13. ስለዚህም ጋድ ወደ ዳዊት ሄዶ፣ “በምድርህ የሦስት ዓመት ራብ ይምጣብህ? ወይስ ጠላቶችህ እያሳደዱህ ሦስት ወር ትሸሽ? ወይስ ደግሞ በምድርህ ላይ የሦስት ቀን ቸነፈር ይምጣ? እንግዲህ አሁን ለላከኝ ምን መልስ እንደምሰጥ አስበህበት ወስን” አለው።

14. ዳዊትም ጋድን፣ “እጅግ ተጨንቄአለሁ፤ ምሕረቱ ታላቅ ስለ ሆነ በእግዚአብሔር እጅ እንውደቅ፤ በሰው እጅ ግን አልውደቅ” አለው።

15. ስለዚህም እግዚአብሔር ከዚያች ዕለት ጥዋት አንሥቶ እስከ ተወሰነው ቀን ድረስ በእስራኤል ላይ ቸነፈር ላከ፤ በዚህም ከዳን እስከ ቤርሳቤህ ድረስ ሰባ ሺህ ሰው አለቀ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ሳሙኤል 24