ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ሳሙኤል 17:22-29 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

22. ስለዚህ ዳዊትና አብሮት ያለው ሕዝብ በሙሉ ተነሥቶ ዮርዳኖስን ተሻገረ፤ ሲነጋም ዮርዳኖስን ሳይሻገር የቀረ አንድም ሰው አልነበረም።

23. አኪጦፌልም ምክሩን እንዳልተከተሉት ባየ ጊዜ፣ አህያውን ጭኖ ቤቱ ወደሚገኝበት ወደ መኖሪያ ከተማው ሄደ፤ ቤቱንም መልክ መልክ ካስያዘ በኋላ በገዛ እጁ ታንቆ ሞተ። በዚህ ሁኔታም ሞቶ በአባቱ መቃብር ተቀበረ።

24. አቤሴሎም ከመላው የእስራኤል ሰዎች ጋር ዮርዳኖስን ሲሻገር፣ ዳዊት ግን መሃናይም ደርሶ ነበር።

25. አቤሴሎምም በኢዮአብ ምትክ አሜሳይን በሰራዊቱ ላይ ሾመ፤ አሜሳይ የእስማኤላዊው የዮቴር ልጅ ነበረ፤ ዮቴርም የኢዮአብን እናት፣ የጽሩያን እኅት፣ የናዖስን ልጅ አቢግያን አግብቶ ነበር።

26. እስራኤላውያንና አቤሴሎም በገለዓድ ምድር ሰፈሩ።

27. ዳዊት መሃናይም ሲደርስ፣ ከአሞናውያን ከተማ ከራባ የመጣው፣ የናዖስ ልጅ ሾቢ፣ ከሎዶባር የመጣው የዓሚኤል ልጅ ማኪርና ከሮግሊም የመጣው ገለዓዳዊው ቤርዜሊ

28. መተኛ ምንጣፎች፣ ወጭቶችና የሸክላ ዕቃዎች ይዘው መጡ፤ እንዲሁም ስንዴና ገብስ፣ ዱቄትና የተጠበሰ እሸት፣ ባቄላና ምስር፣

29. ማር፣ እርጎ፣ በጎችና የላም አይብ እንዲበሉ ለዳዊትና ለሕዝቡ አመጡላቸው፤ ይህን ያደረጉትም፣ “ሕዝቡ በምድረ በዳ ተርቦአል፤ ደክሞአል፤ ተጠምቶአል” በማለት ነው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ሳሙኤል 17