ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

2 ሳሙኤል 17:1-13 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

1. አኪጦፌልም፣ አቤሴሎምን እንዲህ አለው፤ “ዐሥራ ሁለት ሺህ ሰው መርጬ፣ በዛሬዪቱ ሌሊት አባትህን አሳድደዋለሁ፤

2. በደከመውና ዐቅም ባነሰው ጊዜም አደጋ እጥልበታለሁ፤ ሽብር እለቅበታለሁ፤ ከዚያም አብሮት ያለው ሕዝብ ሁሉ ትቶት ይሸሻል፤ ንጉሡን ብቻ እመታዋለሁ፣

3. ሕዝቡን ሁሉ ወደ አንተ እመልሳለሁ፣ አንተ የምትፈልገው የአንድ ሰው ብቻ መሞት ሁሉም እንዲመለሱ ያደርጋል። ከዚያም ሕዝቡ ሁሉ በሰላም ይኖራል።”

4. ምክሩም አቤሴሎምንና አብረውት የነበሩትን የእስራኤልን ሽማግሌዎች ሁሉ ደስ አሰኘ።

5. አቤሴሎም ግን፣ “እስቲ ደግሞ አርካዊውን ኩሲን ጥሩትና የሚለውን እንስማ” አለ።

6. ኩሲ ወደ እርሱ በመጣ ጊዜ አቤሴሎም፣ “አኪጦፌል ይህን ምክር አቅርቦአል፤ ታዲያ እርሱ ያለውን እናድርግ? ካልሆነም እስቲ የአንተን ሐሳብ ንገረን” አለው።

7. ኩሲም አቤሴሎምን እንዲህ አለው፤ “አኪጦፌል የሰጠው ምክር በዚህ ጊዜ የሚያዋጣ አይደለም፤

8. አባትህና ሰዎቹ የማይበገሩ ተዋጊዎችና ግልገሎቿም እንደ ተነጠቁባት የዱር ድብ አስፈሪ መሆናቸውን አንተም ታውቃለህ፤ በተጨማሪም አባትህ በቂ ልምድ ያለው ነው፤ ሌሊቱን ከሰራዊቱ ጋር አያድርም፤

9. እነሆ፤ አሁን እንኳ በአንዱ ዋሻ ወይም በሌላ ቦታ ተደብቆ ይሆናል። እርሱ ቀድሞ አደጋ በመጣል ከሰዎችህ ጥቂት ቢሞቱ ይህን የሰማ ሁሉ፣ ‘አቤሴሎምን የተከተለው ሰራዊት አለቀ’ ብሎ ያወራል።

10. አባትህ ታላቅ ጦረኛ፣ አብረውት ያሉትም ጀግኖች መሆናቸውን እስራኤል ሁሉ ስለሚያውቅ፣ ልቡ እንደ አንበሳ ልብ ነው የተባለው ደፋሩ ወታደር እንኳ በፍርሀት ይርዳል።

11. “እንግዲህ እኔ የምመክርህ ይህ ነው፤ ቍጥሩ እንደ ባሕር ዳር አሸዋ የበዛው፣ ከዳን እስከ ቤርሳቤህ ያለው እስራኤል ሁሉ ወዳንተ ይሰብሰብና አንተው ራስህ ወደ ጦርነቱ ምራው፤

12. ከዚያም እርሱ እገባበት ቦታ ሁሉ ገብተን አደጋ እንጥልበታለን፣ ጤዛ በመሬት ላይ እንደሚወርድ እንወርድበታለን፤ እርሱም ሆነ ሰዎቹ አንድ እንኳ አይተርፉም፤

13. ከአንዲቱ ከተማ ቢገባ፣ እስራኤል ሁሉ ገመድ አምጥቶ አንድ ድንጋይ እንኳ እስከማይቀር ድረስ፣ ከተማዪቱን ወደ ሸለቆ ስበን እንከታታለን።”

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 2 ሳሙኤል 17