ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ዜና መዋዕል 23:24-32 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

24. እንግዲህ እነዚህ የቤተ ሰቡ አለቆች ሆነው እያንዳንዳቸው በየስማቸው ተመዝግበው የተቈጠሩት የሌዊ ዘሮች ናቸው፤ ዕድሜአቸውም ሃያና ከዚያ በላይ የሆናቸው በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ውስጥ የሚያገለግሉ ነበሩ።

25. ዳዊት እንዲህ ብሎ ነበርና፣ “የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር ለሕዝቡ ዕረፍት ሰጥቷል፤ በኢየሩሳሌምም ለዘላለም ለመኖር መጥቷል፤

26. ሌዋውያን ከእንግዲህ ወዲህ ድንኳኑን ወይም የመገልገያ ዕቃውን ሁሉ መሸከም የለባቸውም።”

27. ዳዊት በሰጠው የመጨረሻ መመሪያ መሠረት የተቈጠሩት ሌዋውያን ዕድሜያቸው ሃያና ከዚያ በላይ ነበረ።

28. የሌዋውያኑ ተግባር በእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ አገልግሎት የአሮንን ዘሮች መርዳት፣ የቤተ መቅደሱን ቅጥር ግቢና ክፍሎች መንከባከብ፣ የተቀደሱ ዕቃዎችን ሁሉ ማንጻትና በእግዚአብሔር ቤት ያሉትን ሌሎች ተግባሮች ማከናወን ነበር።

29. እንዲሁም መባ ሆኖ የሚቀርበውን ኅብስተ ገጽ፣ የእህል ቍርባኑን ዱቄት፣ ያለ እርሾ የሚጋገረውን ቂጣ የሚጋግሩ፣ የሚያቦኩና የሚሰፈረውንም ሆነ የሚለካውን ሁሉ በኀላፊነት የሚቈጣጠሩ እነርሱ ነበሩ።

30. በየዕለቱም እግዚአብሔርን ለማመስገንና ለመወደስ ጠዋት ጠዋት ይቆሙ ነበር፤ ይህንንም ማታ ማታ

31. እንዲሁም በየሰንበቱ፣ በወር መባቻ በዓልና በተደነገጉት በዓላት ሁሉ ይፈጽሙ ነበር፤ በተወሰነላቸው ቊጥርና በተሰጠውም መመሪያ መሠረት ዘወትር በእግዚአብሔር ፊት ያገለግሉ ነበር።

32. ስለዚህ ሌዋውያኑ ለመገናኛው ድንኳንና ለመቅደሱ እንዲሁም በወንድሞቻቸው በአሮን ዘሮች ሥር ሆነው ለእግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ያለባቸውን ኀላፊነት ያከናውኑ ነበር።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ዜና መዋዕል 23