ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ነገሥት 22:20-36 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

20. እግዚአብሔርም፣ “በገለዓድ በምትገኘው ሬማት ላይ ዘምቶ እዚያው እንዲሞት፣ አክዓብን ማን ያስተው?” አለ።’“ታዲያ አንዱ ይህን፣ ሌላውምያን አለ፤

21. በመጨረሻም፣ ‘አንድ መንፈስ ወጣ፤ ከዚያም በእግዚአብሔር ፊት ቆሞ፣ “እኔ አስተዋለሁ” አለ።’

22. እግዚአብሔርም፣ ‘እንዴት አድርገህ?’ ሲል ጠየቀው።“እርሱም፣ ‘እኔ እወጣለሁ፤ በገዛ ነቢያቱም አፍ ሁሉ የሐሰት መንፈስ እሆናለሁ’ አለ። እግዚአብሔርም፣ “በል እንግዲያው ውጣና አስተው፤ ይሳካልሃል” አለው።

23. “ስለዚህ እነሆ እግዚአብሔር በእነዚህ ሁሉ ነቢያትህ አፍ የሐሰት መንፈስ አኖረ፤ በአንተም ላይ መዓቱን እንደሚያመጣብህ ተናገረ።”

24. ከዚያም የክንዓና ልጅ ሴዴቅያስ ወጥቶ ሚክያስን በጥፊ መታውና፣ “ለመሆኑ የእግዚአብሔር መንፈስ ከእኔ በየት በኩል ዐልፎ ነው አንተን መጥቶ ያናገረህ?” ሲል ጠየቀው።

25. ሚክያስም፤ “ይህንማ ለመደበቅ ወደ አንዲት እልፍኝ በሄድህ ዕለት ታውቀዋለህ” አለው።

26. ከዚያም የእስራኤል ንጉሥ እንዲህ ሲል አዘዘ፤ “በሉ ሚክያስን ይዛችሁ ወደ ከተማዪቱ ገዥ ወደ አሞንና ወደ ንጉሡ ልጅ ወደ ኢዮአስ መልሱት፤

27. ከዚያም፣ ‘ንጉሡ፣ “በደኅና እስክመለስ ድረስ፣ ይህን ሰው በእስር ቤት አቈዩት፤ ከደረቅ እንጀራና ከውሃ በስተቀር ሌላ እንዳትሰጡት” ብሎአል በሉት’ አለ።

28. ሚክያስም፣ “አንተ በደኅና ከተመለስህ እግዚአብሔር በእኔ አልተናገረማ!” አለ፤ ከዚያም በመቀጠል፣ “በዚህ ያለኸው ሕዝብ ሁሉ ይህን ቃሌን ልብ ብለህ ያዘው፤” አለ።

29. ስለዚህ የእስራኤል ንጉሥና የይሁዳ ንጉሥ ኢዮሣፍጥ በገለዓድ ወደምትገኘው ሬማት ወጡ።

30. የእስራኤል ንጉሥ ኢዮሣፍጥን፣ “እንዳልታወቅ እኔ ልብስ ለውጬና ሌላ ሰው መስዬ እገባለሁ፤ አንተ ግን ልብሰ መንግሥትህን ልበስ” አለው። ስለዚህ የእስራኤል ንጉሥ ራሱን ደብቆ ወደ ጦርነቱ ገባ።

31. በዚህ ጊዜ የሶርያ ንጉሥ ሠላሳ ሁለቱን የሠረገላ አዛዦች፣ “ከራሱ ከእስራኤል ንጉሥ በቀር ትንሽም ይሁን ትልቅ ከማንም ጋር እንዳትገጥሙ” ሲል አዞአቸው ነበር፤

32. የሠረገላ አዛዦቹ ኢዮሣፍጥን ሲያዩት፣ “ያለ ጥርጥር ይህ የእስራኤል ንጉሥ ነው” አሉ፤ ስለዚህ አደጋ ሊጥሉበት ከበቡት፤ ኢዮሣፍጥ ሲጮህ ግን

33. የሠረገላ አዛዦቹ እርሱ የእስራኤል ንጉሥ አለመሆኑን አውቀው መከታተሉን ተዉት።

34. ነገር ግን አንዱ ቀስቱን ሳያልም እንዲሁ ሲያስፈነጥር በጦር ልብሱ መጋጠሚያ ላይ የእስራኤልን ንጉሥ ወጋው፤ ንጉሡም ሠረገላ ነጂውን፣ “ቈስያለሁና ወደ ኋላ አዙረህ ከጦሩ ሜዳ አውጣኝ” አለው።

35. ጦርነቱም ቀኑን ሙሉ ተፋፍሞ ዋለ፤ በዚህ ጊዜም ንጉሡ በሶርያውያን ፊት ለፊት ሠረገላው ላይ ቀና ብሎ እንደ ተደገፈ ነበር፤ የቊስሉ ደም በሠረገላው ወለል ላይ ይወርድ ነበር፤ በዚያኑ ዕለት ማታም ንጉሡ ሞተ።

36. ፀሓይ ስትጠልቅም በሰራዊቱ መካከል፣ “እያንዳንዱ ሰው ወደ ቤቱ፣ እያንዳንዱም ወደ ሀገሩ ይሂድ!” የሚል ጩኸት አስተጋባ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ነገሥት 22