ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ሳሙኤል 28:12-25 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

12. ሴትዮዋም ሳሙኤልን ባየችው ጊዜ በታላቅ ድምፅ ጮኽች፤ ሳኦልንም፣ “አንተ ሳኦል ሆነህ ሳለ፣ ለምን አታለልኸኝ?” አለችው።

13. ንጉሡም፣ “አትፍሪ፤ ለመሆኑ ምን እያየሽ ነው?” አላት።ሴትዮዋም፣ “አንድ መንፈስ ከምድር ሲወጣ አያለሁ” አለችው።

14. እርሱም፣ “መልኩ ምን ይመስላል?” ሲል ጠየቃት።እርሷም፣ “ካባ የለበሰ አንድ ሽማግሌ ሰው እየወጣ ነው” አለችው።ሳኦልም ሴትዮዋ ያየችው ሳሙኤል መሆኑን ዐወቀ፤ በመሬትም ላይ ተደፍቶ እጅ ነሣ።

15. ሳሙኤልም ሳኦልን፣ “አስነሥተህ የምታውከኝ ለምንድ ነው?” አለው።ሳኦልም፣ “እጅግ ተጨንቄአለሁ፤ ፍልስጥኤማውያን እየወጉኝ ነው፤ እግዚአብሔርም ከእኔ ርቆአል፤ በነቢያትም ሆነ በሕልም አልመለሰልኝም፤ ስለዚህ ምን ማድረግ እንደሚገባኝ እንድትነግረኝ ጠራሁህ” አለው።

16. ሳሙኤልም እንዲህ አለ፤ “ታዲያ እግዚአብሔር ከራቀህ፣ ጠላትም ከሆነህ ለምን ትጠይቀኛለህ?

17. እግዚአብሔር በእኔ የተናገረውን አድርጎአል፤ እግዚአብሔር መንግሥትህን ከእጅህ ነጥቆ ለጎረቤትህ ለዳዊት ሰጥቶታል።

18. ለእግዚአብሔር ስላልታዘዝህ፣ ታላቅ ቊጣውንም በአማሌቃውያን ላይ ስላል ፈጸምህ እግዚአብሔር ዛሬ ይህን አድርጎብሃል።

19. እግዚአብሔር አንተንና እስራኤልን ለፍልስጥኤማውያን አሳልፎ ይሰጣል፤ አንተና ልጆችህም ነገ ከእኔ ጋር ትሆናላችሁ፤ እንዲሁም እግዚአብሔር የእስራኤልን ሰራዊት ለፍልስጥኤማውያን አሳልፎ ይሰጣል።”

20. ሳሙኤል ከተናገረው ቃል የተነሣ፣ ሳኦል በፍርሀት ተውጦ ወዲያውኑ በቁመቱ ሙሉ መሬት ላይ ወደቀ፤ ቀኑንና ሌሊቱን ሁሉ እህል ስላልቀመሰ ጒልበቱ ዝሎ ነበር።

21. ሴትዮዋ ወደ ሳኦል መጥታ እጅግ መደንገጡን ባየች ጊዜ እንዲህ አለችው፤ “እነሆ፤ አገልጋይህ ቃልህን ሰምቻለሁ፤ በነፍሴም ቈርጬ የነገርኸኝን ፈጽሜአለሁ።

22. አሁንም እባክህ አገልጋይህ የምትልህን ስማ፤ ብርታት አግኝተህ መሄድ እንድትችል፣ ጥቂት ምግብ ላቅርብልህና ብላ።”

23. እርሱም፣ “አልበላም” በማለት እምቢ አለ።ነገር ግን የራሱ ሰዎች ከሴትዮዋ ጋር ሆነው አጥበቀው ስለ ለመኑት ቃላቸውን ሰማ፤ ከመሬትም ተነሥቶ በዐልጋ ላይ ተቀመጠ።

24. ሴትዮዋም በቤቷ የሠባ ጥጃ ስለነበራት፣ፈጥና ዐረደችው፤ ዱቄት ወስዳ ለወሰች፣ እርሾ የሌለው እንጀራም ጋገረች።

25. ከዚያም ለሳኦልና ለሰዎቹ አቀረበችላቸው፤ እነርሱም በሉ፤ በዚያም ሌሊት ተነሥተው ሄዱ።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ሳሙኤል 28