ብሉይ ኪዳን

አዲስ ኪዳን

1 ሳሙኤል 19:14-24 መጽሐፍ ቅዱስ፥ አዲሱ መደበኛ ትርጒም (NASV)

14. ሳኦል ዳዊትን እንዲይዙት ሰዎች በላከ ጊዜ ሜልኮል፣ “እርሱ ታሞአል” አለቻቸው።

15. ሳኦልም ሰዎቹ ዳዊትን እንዲያዩት መልሶ ላካቸው፤ እርሱም፣ “እገድለው ዘንድ ከነዐልጋው አምጡልኝ” አላቸው።

16. የተላኩትም ሰዎች በገቡ ጊዜ እነሆ፤ የጣዖት ምስሉ በዐልጋው ላይ ተጋድሞ በራስጌውም የፍየል ጠጒር ተደርጎለት ነበር።

17. ሳኦልም ሜልኮልን፣ “እንዲህ አድርገሽ ያታለልሽኝ፣ ጠላቴ እንዲያመልጥ የሰደድሽው ለምንድን ነው?” ሲል ጠየቃት።ሜልኮልም፣ “ ‘እንዳመልጥ እርጂኝ፤ ያለዚያ እገድልሻለሁ’ አለኝ” ብላ መለሰችለት።

18. ዳዊት ሸሽቶ ካመለጠ በኋላ፣ ወደ አርማቴም ወደ ሳሙኤል ሄደ፣ ሳኦል ያደረገበትን ሁሉ ነገረው። ከዚያም እርሱና ሳሙኤል ወደ ነዋት ሄደው ተቀመጡ።

19. ለሳኦልም፣ “እነሆ፤ ዳዊት በአርማቴም በምትገኘው በነዋት ተቀምጦአል” ብለው ነገሩት።

20. ስለዚህ ዳዊትን እንዲይዙ ሰዎችን ላከ፤ ይሁን እንጂ፣ የነቢያትም ጉባኤ በሳሙኤል መሪነት ትንቢት ሲናገሩ ባዩ ጊዜ፣ የእግዚአብሔር መንፈስ በሳኦል ሰዎች ላይ ወረደ፤ እነርሱም እንደዚሁ ትንቢት ተናገሩ።

21. ሳኦልም ይህ በተነገረው ጊዜ ሌሎች ሰዎች ላከ፤ እነርሱም ትንቢት ተናገሩ፤ ሳኦል ለሦስተኛ ጊዜ ሰዎች ላከ፣ እነርሱም ደግሞ ትንቢት ተናገሩ።

22. በመጨረሻም፣ እርሱ ራሱ ወደ አርማቴም ሄደ፤ ከዚያም በሤኩ ወዳለው ትልቅ የውሃ ማጠራቀሚያ ጒድጓድ እንደ ደረሰ፣ “ሳሙኤልና ዳዊት የት ናቸው?” ሲል ጠየቀ።አንድ ሰውም “በአርማቴም በምትገኘው በነዋት ዘራማ ናቸው” ብሎ ነገረው።

23. ስለዚህ ሳኦል በአርማቴም ወደምትገኘው ወደ ነዋት ዘራማ ሄደ፤ የእግዚአብሔር መንፈስ በእርሱም ላይ ደግሞ ወረደ፤ ወደ ነዋት እስኪደርስ ድረስም ትንቢት እየተናገረ ተጓዘ።

24. እርሱም ልብሱን አውልቆ፣ በሳሙኤልም ፊት ደግሞ ትንቢት ተናገረ፤ በዚህ ሁኔታም ቀኑንና ሌሊቱን በሙሉ ራቁቱን ተጋደመ። ሕዝቡ፣ “ሳኦልም ደግሞ ከነቢያት እንደ አንዱ ሆኖ ተቈጠረ?” ያለው በዚህ ምክንያት ነው።

ሙሉ ምዕራፍ ማንበብ 1 ሳሙኤል 19